May o5,2019

በያሬድ ሃይለማሪያም

በብሔር መደራጀት መብትህ ነው። ባህልህን፣ ቋንቋህን፣ ታሪክህን እና ሌሎች የማንነትህ መገለጫ የሆኑ እሴቶችህን የማጎልበት እና ጠብቆ ለትውልድ ለማስተላለፍ መሰባሰብ እና የበኩልህን ማበርከት መብት ብቻም ሳይሆን የትውልድ ግዴታህም ነው። አንተ የተውከውን ባህልህን፣ ቋንቋህን እና እምነትህን ትውልድ አይረከበውም። የሁሉም ብሔረሰብ ባህል፣ ቋንቋ እና ታሪካዊ ትውፊቶች ናቸው አንድ ላይ ሆነው ኢትዮጵያን ኢትዮጵያ የሚያሰኟት። ባለንበት ሥልጡን ዘመን ባህልን፣ ቋንቋን እና ሌሎች የማንነት መገለጫ ትውፊት የሆኑትን ሃብቶችህን ለማስጠበቅ የደም ግብር አያስፈልግም። አለም የደረሰበት ሥልጣኔ ማንንም ሳትገድል፤ እራስህንም በከንቱ ደመ ከልብ ሳታደርግ ከነ ባህልህ እና ቋንቋህ የምትበለጽግበት እና እንደ እንቁ የምትደምቅበት ዘመን ላይ ነህ ያለኽው።

ከትምህርትም ዘመናዊ ትምህርት ቀስመኽ፣ ሳይንሳዊ ምርምር በሚካሄድባቸው የእውቀት መፍለቂያ ተቋማት ውስጥ አልፈህ፣ እንደ ዘመኑ ሰው ሌላው አለም የተጫማውን ተጫምተህ፣ የለበሰውን ለብሰህ፣ የቴክኖሎጂው ተጠቃሚም ሆነህ እንደ ባቢሎን ዘመን ሰው ማሰብህ ምነዋ? የምትጣላበት ብታጣ በመቶ አመታት ወደ ኋላ እያየህ እንዲህ ነበርኩ፣ እንዲያ ነበርክ እየተባባልክ ዛሬህን የምታጨልም ጉድ ፍጥረት መሆንስ ምነዋ? አንተ በጎነጎንከው የዘር ፖለቲካ በልቶ ያልጠገበው ወገንህ በየጥሻው እየታረደ ሲጣል እና ከቅዮው እየተፈናቀለ በየዱሩ ሲንከራተት እያየህ ከመጸጸት ይልቅ ሞቱን እየደገስክ በግፍ ክምር የምትቆታች ግፈኛ መሆንህስ ምነዋ? በዘመናዊ እውቀት ታግዘህ ከድህነት አረንቋ ታላቅቀኛለህ ቦሎ በተስፋ ሲጠብቅህ ለኖረው ድሃ የአገርህ ልጅ ውለታውን እምትከፍለው እረብ በሌለው የፖለቲካ ንትርክ ሰክረህ በሞቱ በመዘባበት ነው ውይ?

ልንገርህ ወዳጄ፤

ብሔረተኝነት በራሱ አግላይ ነው። ስታከረው እና የፖለቲካ ፍላጎትህ ማሳለጫ መንገድ ስታደርገው ከአግላይነቱም አልፎ ሌላውን ሰው በቃላት እና በድርጊት ለማጥቃት በር ይከፍታል። አግላይ የሆነው ብሔረተኝነት በብዙ አገራት በተለይም በምዕራቡ አለም ጨምሮ አለ። መገለጫው የቆዳ ቀለም፣ የዘር ግንድ፣ የቋንቋ ወይም ኃይማኖት ላይ ያነጣጠረ ሊሆን ይችላል። ብሔረተኝነት ከአግላይነት ወደ ጥቃት የሚሸጋገረው ግን በተወሰኑ ስፍራፎች ብቻ ነው። ይኽውም የሕግ የበላይነት ባልሰፈነበት ወይም በሥልጣን ላይ ያለው አካል ጭምር እራሱ የብሔር መድሎዎን ደጋፊ እና አራማጅ በሆነበት ወይም ሥርዓት አልበኝነት ነግሶ አክራሪ ቡድኖች ከመንግስት በላይ አቅም ባገኙበት ስፍራ ብቻ ነው።

አውሮፓ ውስጥ ስር የሰደደ ዘረኝነት አለ። ዘረኝነቱ በማግለል እና በመድሎ ደረጃ በየቦታው ይታያል። ይሁን እና ዘረኝነትን የሚጠየፍ፣ እንደ ወንጀል የሚቆጥር እና የማያበረታታ ማህበረሰብ፣ ፖለቲካዊ ሥርዓት እና መንግስት ስላለ ዘረኞቹ ሊደራጁ ይችላሉ ነገር ግን የማንንም መብት ሊጥሱ እና ማንም ላይ በቃላትም ሆነ በድርጊት ጥቃት ሊሰነዝሩ አይችሉም። ይህን ያደረገ ሰው በሕግ ይጠየቃል። ስለዚህ የናዚ ደጋፊዎች ባሉበት እና አክራሪ ዘረኞች ባሉበት መንደር ሳይቀር ከአፍሪቃም ሆነ ከሌላው አለም የመጣ ሰው ደረቱን ነፍቶ ይኖራል። በሰላም ውሎ በሰላም ያድራል። ዘረኛውም መጤዎቹን ወይም የማይፈልጋቸውን ሰዎች እያየ እና ውስጥ ውስጡን እየተቃጠለ ከማጉረምረም ባለፈ ምንም ማድረግ አይችልም። ይህ ማላት ግን አልፎ አልፎ ችግር አይኖርም ማለት አይደለም። ነገር ግን ከሕግ ማዕቀፍ አይወጣም።

በአገራችን እየከረረ የመጣው ብሔረተኝነት መስመሩን ከሳተ ውሎ አድሯል። ከህግ ቁጥጥርም ውጭ ወጥቷል። ለዚህም ሁለት ነገሮች አስተዋጽኦ አድርገዋል። አንደኛው መንግስት ሕግ በማስከበሩ እና የሕግ የበላይነትን በማስፈኑ እረገድ ያሳየው ዳተኝነት ነው። ሁለተኛው እና አሳሳቢው ጉዳይ ደግሞ አክራሪ ብሔረተኞችን የሚጠየፍ እና በአደባባይ የሚያወግዝ ማህበረሰብ ገና አለመፈጠሩ እና በተቃራኒው አክራሪ ብሔረተኞች ባዘጋጁለት የብሔር ወጥመድ ውስጥ የሚገባው ሰው ቁጥር እለት ከዕለት እየጨመረ መምጣቱ ነው። አክራሪ ብሔረተኞች ብቻቸውን መቆም ስለማይችሉ የመጀመሪያው ስልታቸው ሁሉንም ብሔረተኛ ማድረግ ነው። ሁሉም በየብሔሩ ከተሸጎጠ አገራዊ አስተሳሰብ ይከስማል። ያኔ አገርን ለማፍረስም ሆነ ብሔረተኞች በቀደዱት ቦይ ለመንጎድ መንገዱ ቀና ነው።

አሁን ካለንበት አደጋ ልንወጣ እና አገሪቱም የአክራሪ ብሔረተኞች መፈንጫ እንዳትሆን ማድረግ የሚቻለው፤

ያኔ ኢትዮጵያ የሁሉም ኢትዮጵያዊ ትሆናለች። በግፉአን ደም መቆታቸቱ ይብቃ!

ቸር እንሰንብት!

አቶ ያሬድ ሃይለማሪያም፣ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች