October 30, 2019

Seyoum Teshome  — በአንዲት ቀዳዳ አሾልቆ የህወሃቶችን ቤት ማየት እንዴት ደስ ይላል? ምክንያቱም ወደ ቅጥር ግቢው የማይመጣ ሰው የለም። ያረጀ አስተሳሰብ ያላቸው ወጣት አመራሮች፣ ያፈጀ የፖለቲካ አመለካከት የሚያራምዱ የድርጅቱ መስራቾች፣ ከአዲስ አበባ እስከ ዋሽንግተን ያሉት የህወሓት አፈ-ቀላጤዎች፣ “አንጃ” ተብለው ከድርጅቱ የተባረሩ የቀድሞ ባለስልጣናትና የጦር አዛዦች፣ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እያስተማሩ ለህወሓቶች የሚሰልሉ ገለልተኛ መሳይ “ምሁራን”፣ የገንዘብ ምንጫቸው የደረቀባቸው “ጋዜጠኞች”፣ አድማጭ የጠረረባቸው ወሬ አቀባዮች፣ በአቋራጭ ያገኙት ዕውቅና የጠፋባቸው ሰዎች፣ አየር በአየር ንግድ የቀረባቸው “ነጋዴዎች”፣ በብሔር ኮታ ስልጣን ያገኙ የኢህአዴግ አመራሮች… ወዘተ። በአጠቃላይ ህወሓቶች ጋር የማይመጣ ሰው የለም።

በባህሪያቸው ህወሓቶች አጮልቆ የሚያያቸውን ሰው አምርረው ይጠላሉ። ምክንያቱም የሚያወሩትን፣ የሚያስቡትን ብሎም የሚያደርጉትን ነገር ከማንም በላይ ራሳቸው ያውቃሉ። እኛ ደግሞ ከህወሓቶች ቤት ወጪና ገቢውን አጮልቀን እናያለን። ጆሯች ለጥፈን የሚያወሩትን እናዳምጣለን። ከዛም በቀጣይ ሊያደርጉ ያሰቡትን ሸርና አሻጥር ቀድመን እናጋልጣለን። ወ/ሮ አዜብ መስፍን ከህወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ከተባረረችበት ዕለት አንስቶ ያደረጉትን ብቻ ሳይሆን ገና ሊያደርጉ ያሰቡትን ነገር ቀድመን እነጋልጣለን።

የኢህአዴግ ውህደት ከህወሓቶች በላይ ያስጨነቀው አካል የለም። የእነሱ አገልጋይና ተላላኪ የነበሩት የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ውህደት በመፈፀም አንድ ፓርቲ ለመሆን የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ለህወሓቶች የህልውና አደጋ ነው። ህወሓቶች ውህደቱን ቢቀላቀሉ በውስጡ ቀልጠው ይቀራሉ። በመሆኑም እንደ ቀድሞ የኢትዮጵያን ፖለቲካና ኢኮኖሚ በበላይነተት መቆጣጠር አይችሉም። ስለዚህ ውህደቱን ፈፅሞ መቀላቀል አይሹም። ከውህደቱ ወጥተው ደግሞ ራሳቸውን ችለው መንቀሳቀስ አይችሉም። ምክንያቱም ከኢህአዴግ ከወጡ ራሳቸውን ወደ ክልል ፓርቲነት ያወርዳሉ። የትግራይ ክልል በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ውስጥ ያለው የወንበር ብዛት እንኳን የፌደራል መንግስትን ስልጣን ጠቅልሎ ለመያዝ ከአጋርነት የሚያልፍ አይደለም። ያለ ኢህአዴግ ህወሓት ጎማ የሌለው መኪና ነው። ስለዚህ ለህወሓት ከኢህአዴግ መውጣትም ሆነ መዋሃድ ራስን በራስ እንደማጥፋት ነው።

በዚህ መሰረት ህወሓት ያለው ብቸኛ አማራጭ የኢህአዴግን ውህደት ማደናቀፍ ነው። ለዚህ ደግሞ ከ2011 ዓ.ም አጋማሽ ጀምሮ የተግባር ዕቅድ በማውጣት ሲንቀሳቀሱ እንደነበር ይታወቃል። ዕቅዱ ሦስት ዋና ዋና ተግባራትን ያካተተ ነው። እነሱም አንደኛ፡- ኢህአዴግን እንደ መታገያ መድረክ በመጠቀም ውህደቱን ማደናቀፍ፣ ሁለተኛ፡- ብሔርተኛ ቡድኖችን አንድ ላይ በማሰባሰብ የፌደራሊስቶች ግንባርን መፍጠርና የኢህአዴግ ተቀናቃኝ መሆን፣ ሦስተኛ፡- በተለያዩ የሀገሪቱ አከባቢዎች ካሉ ብሔርተኛ ቡድኖች በመመሳጠር ህዝባዊ አመፅና ተቃውሞ በመቀስቀስ የፖለቲካ ቀውስና አለመረጋጋት መፍጠር የሚሉት ናቸው። ባለፉት ስምንት ወራት እነዚህን ተግባራት በተቀናጀ መልኩ ቢያከናውኑም የሚፈለገው ውጤት ሊመጣ አልቻለም።

በተለይ ሰሞኑን ከአቶ ጃዋር መሃመድ ጋር በመሆን የተጫወቱት የአጋች-ታጋች ድራማ የዕቅዱ የመጨረሻ ክፍል ነው። ነገር ግን ህወሓቶች ዕቅዳችን አልተሳካም ብለው እጃቸውን ሰብስበው የሚቀመጡ ዓይነት አይደሉም። እየሄዱበት ያለው የጥፋት መንገድ ሀገርና ህዝብን ከፍተኛ ዋጋ እያስከፈለ እንደሆነ ወይም ደግሞ አካሄዳቸው በተጨባጭ እውነታ ላይ የተመሰረተ አለመሆኑን ተገንዝበው የማስተካከያ ለውጥ ከማድረግ ይልቅ በተለመደው የሴራ ፖለቲካ መቀጠል መርጠዋል። በዚህ መሰረት ሦስት ዋና ዋና ተግባራት ያሉት አዲስ ዕቅድ አዘጋጅተዋል።

ዕቅዱ በዋናነት የሀገሪቱ ህዝብ በዶ/ር አብይ በሚመራው መንግስት ላይ ያለውን እምነት እንዲያጣ በማድረግ ላይ የተመሰረተ ነው። በእቅዱ የሚከናዎኑ ሦስት ዋና ዋና ተግባራት ደግሞ የሚከተሉት ናቸው። አንደኛ፡- ብዛት ያላቸው መፅሃፍትን ማፃፍና ማሳተም፣ ሁለተኛ፡- በከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎች ላይ የስም ማጥፋት ዘመቻ መክፈት፣ ሦስተኛ፡- የተቀነባበሩ ግድያ ሙከራዎችን ማካሄድ ናቸው። በእርግጥ እነዚህ ተግባራት ከአንድ የፖለቲካ ድርጅት የሚጠበቁ አይደሉም። ከዚያ ይልቅ ህወሐት ለረጅም ግዜ ሲጠቀምባቸው የነበሩ ስልቶች ናቸው። ለምሳሌ ባለፈው አመት “የተጠለፈው ትግል” በሚል ርዕስ የወጣው መፅሃፍ በህወሓቶች የገንዘብ ድጋፍ የታተመ ስለመሆኑ አፈትልኮ በወጣው የአቶ ዘርዓይ አሰግዶም ኢሜይል ውስጥ ጠቋሚ መረጃዎች ተገኝተዋል።

አዲስ በወጣው ዕቅድ መሰረት የህወሓት አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች በዋናነት ከላይ በተጠቀሱት ዋና ዋና ተግባራት ላይ ትኩረት ያደርጋሉ። የመጀመሪያው የተጀመረውን ለውጥ እና የዶ/ር አብይ አመራርን የሚያጣጥል፣ የኢህአዴግን ውህደት የሚያጠለሽ፣ በህዝቦች መካከል ያለመተማመንና ጥርጣሬ ስሜት የሚፈጥር፣ እንዲሁም በተለያዩ አከባቢዎች የብሔር ግጭትና ሁከት የሚቀሰቅስ ይዘት ያላቸው መፅሃፍት በብዛት ታትመው ገበያ ላይ ይቀርባሉ። ሁለተኛ በማህበራዊ ሚዲያዎች አማካንኝነት በተለያየ ደረጃ በሚገኙ የመንግስት ኃላፊዎች ላይ የስም ማጥፋት ዘመቻ ይከፈታሉ። በተለይ በኢህአዴግ አመራሮች መካከል ግጭትና አለመግባባት እንደተፈጠረ በመጥቀስ፣ ስለ አመራሮቹ የግልና ቤተሰባዊ ጉዳዮች የሃሰት መረጃዎችን በስፋት በማህበራዊ ሚዲዎች ላይ ያወጣሉ። ሦስተኛው የተግባር ዕቅድ ደግሞ የተቀነባበረ የግድያ ሙከራዎችን ማድረግ ነው። በዚህ ረገድ በከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎች፣ ታዋቂ ግለሰቦች፣ የሃይማኖትና የፖለቲካ መሪዎች፣ እንዲሁም በማህብረሰቡ ዘንድ ሽብርና ፍርሃት፣ እንዲሁም አለመግባባትና ግጭት ሊፈጥር በሚያስችል መልኩ የግድያ ሙከራዎች ያደርጋሉ።

ከላይ የተጠቀሱት ህወሓት በቀጣይ የሚያከናውናቸው ዝርዝር ተግባራት ናቸው። እነዚህ ተግባራት ደግሞ የህወሓት በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ የሚከተለው ስትራቴጂክ ዕቅድ አካል ናቸው። ይህ ዕቅድ ህወሓት ከአዲስ አበባ ሸሽቶ መቀሌ ከመግባቱ በፊት የነደፈው ስትራቴጂ ነው። በእርግጥ ህወሓሓ ከውሸትና ስም ማጥፋት አልፎ በግልፅ በሽብር ተግባር ውስጥ ይሰማራል ብሎ ማሰብ ለብዙዎች እውነት የማይመስል ነገር ነው። ቀንደኛ የህወሓት አባላትና ደጋፊዎች ግን የዕለት ከዕለት እንቅስቃሴያቸው አካል ነው። በተለይ በማህበራዊ ሚዲያዎች የሚፅፏቸው ነገሮች በሙሉ የዕቅዱ አካል ናቸው።

ለምሳሌ ፍፁም ብርሃኔ ድሬ የተባለው ቀንደኛ የህወሓት አክቲቪስት በአደማ ከተማ ውጥረት በነገሰበት ሰዓት በፌስቡክ ገፁ ላይ ያወጣውን አንድ ፅሁፍ እንደ ማሳያ መጥቀስ ይቻላል። የፅሁፉ ይዘት በአዳማ ከተማ ሁከትና ብጥብጥ እንዲነሳ የነበረውን ፍላጎት በግልፅ ያሳያል። ይሄ ደግሞ የፍፁም ብቻ ሳይሆን የህወሓት አባላትና አመራሮች የጋራ አቋም ነው። ይህ አቋም ደግሞ ከላይ በተጠቀሰው የህወሓት ስትራቴጂክ ዕቅድ ላይ በግልፅ የተቀመጠ ነው። ለዚህ ደግሞ ሌላ ቦታ መሄድ ሳያስፈልግ ራሱ ፍፁም ብርሃኔ ገፅ ላይ እናገኘዋለን። ሁለት አመት ወደ ኋላ ተመልሰን እ.አ.አ. በሰኔ 22/2017 ዓ.ም ፍፁም ብርሃኔ በፌስቡክ ገፁ ላይ ያወጣውን ፅሁፍ ብንመለከት እንዲህ ይላል፤

“ህወሓት አራት ኪሎ ቤተመንግስትን ለቅቃ ወደ መቀሌ ከተመለሰች፣ የኦሮሞ ብሔርተኞች ስልጣን ከያዙ፣ በኦሮሚያ ክልል የሚኖረውን ህዝብ ያፈናቅላሉ፣ በአሰቃቂ ሁኔታ ይገድላሉ፣ ሀብት ንብረት ይዘርፋሉ፣ የሃይማኖት ተቋማትን ያወድማሉ፣ ቀጠናውንም የእስላም ሀገር ለመመስረት የሞክራሉ፣ በመጨረሻ ግን ጉዳቱ ለእነርሱ ነው። Mark my word!”

ባለፈው ሐሙስ አዳማ ላይ ውጥረት መንገሱን ተከትሎ “ኢዜማ በከተማው የራሱን ሴል አደራጅቶ ጨርሷል። ልክ እንደ 97ቱ በ52 ቦታዎች ላይ አመፅ ለማስነሳት ራሱን አደራጅቷል” በማለት ሁከትና ብጥብጥ ለመቀስቀስ ጥረት ማድረጉነ እንደ አንድ የህወሓት አባል ከእሱ የሚጠበቅ ነው። ነገር ግን ባለፈው ሳምንት ዕሮብ ዕለት በተለያዩ የኦሮሚያ አከባቢዎች የተፈፀሙትን አሰቃቂ ድርጊቶች ፍፁም ብርሃኔ የዛሬ ሁለት አመት ሰኔ 2009 ላይ ቆሞ ከታየው ነገሩ ሌላ ነው። በእርግጥ ፍፁም ብርሃኔ የተማረው የፖለቲካ ሳይንስ አይደለም። ሌላው ቀርቶ የሰለጠነበት የትምህርት ዘርፍ እንኳን ማህበራዊ ሳይንስ አይደለም። ፍፁም ሃሮማያ ዩኒቨርሲቲ ገብቶ ያጠናው የግብርና ኢኮኖሚክስ ነው። ከዚህ በተረፈ በራሱ ጥረት የፖለቲካ መፅሃፍት አንብቦ ጥልቅ የሆነ ትንታኔ ሲሰጥ አይተን አናውቅም። በሌላ በኩል እንደ አባባ ታምራት ጠንቋይ አይደለም። አሊያም ደግሞ “ጠንቋይ ነኝ” ብሎ ሲናገር አልሰማንም። መቼም አንድ ጭፍን የህወሓት ደጋፊ “መጪው ግዜ የሚታየኝ መሲህ ነኝ” ሊል አይችልም።

በአጠቃላይ በዚህ ሰሞን የሆነው ነገር እንኳን ለመናገር ለማሰብ እንኳን የሚከብድ ነው። ፍፁም ብርሃኔ ግን ሰኔ 2009 ላይ ቆሞ ባሳለፍነው ሳምንት የሆነውን አንድ በአንድ ዘርዝሮ ፅፏል። ብዙዎች በእውን አይተው በቃል ለመናገር የከበዳቸውን ነገር እሱ ከሁለት አመት በፊት በዝርዝር መግለፁ የሚያሳየው ሁለት ነገር ነው። አንደኛ፡- ፀሃፊው ራሱ ድርጊት ፈፃሚ ነው። ሁለተኛ፡- ድርጊቱ የተፈፀመው ከሁለት አመት በፊት በወጣ ዕቅድ መሰረት ነው። ከላይ በተገለፀው መሰረት ሁለተኛው ሃሳብ ትክክል ነው። ባለፈው ሳምንት ሌሎች ቀንደኛ የህወሓት አባላትና ደጋፊች ሲያወጧቸው የነበሩትን ፅሁፎች የሚያሳዩት ይሄንኑ ነው።

Source -EthioThinkTank