October 10, 2014
ከአንሙት
ጸጋዬማ ጸጋችን ነው፣
አብሮን ያለ፣ እኛም ያለነው፣
ተምሳሌት የትውልዳችን፣
የሆነ፣ ሆኖ ያየነው፣
ውስጥ ያለ፣ በልቦናችን፣
እስካለን የምናኖረው፣
ለልጆች፣ ልጅ ልጆቻችን፣
አደራ የምንሰጠው፣
የሰው መሆን መገለጫችን፣
አድርገን የምናወርሰው፣
ጸጋዬማ ጸጋችን ነው!
ጸጋዬማ ጸጋችን ነው፣
በመኖራችን የሚኖር፣
ስታፍኑት የሚናገር፣
ስታሥሩት ፈቶ ‘ሚበር፣
ስታጨልሙት የሚያበራ፣
በብሩህ መንገድ የሚመራ፣
ፋኖ መሪ፣ የጀግና አውራ፣
ለሞቱ ድግስ የሚያቅራራ፣
የትውልድ ፈርጥ፣ ‘ሚያኮራ!
ጸጋዬማ ነው ጸጋችን፣
የትውልድ ቅርስ ሞገሳችን፣
የዘመናት መሻገሪያ፣
የመድረሻ ድልድያችን፣
ከጨለማ ወደ ንጋት፣
የሚመራ መብራታችን፣
አቅም ሲያጥጥ ምርኩዛችን፣
የተሥፋ ምንጨ መጽናኛችን፣
ፋና ወጊ ኮከባችን፣
ጸጋዬማ ነው ጸጋችን!
ጸጋዬማ ጸጋችን ነው!
ቆሌ ርቆ ተጣልቷችሁ፣
ቋት አይሞላ ዕውነታችሁ፣
ማተብ አልባ አንገታችሁ፣
ነቁጥ ይሉኝታም የሌላችሁ፣
ጭብጥ እልም የለው ዕይታችሁ፣
ውሃ አይቋጥር ንባባችሁ፣
ኪሎ አይደፋ ምግባራችሁ፣
የእኛ ጸጋ፣
ለእናንት ህመም ሆኖባችሁ
እሱነቱ ቢያስፈራችሁ፣
ሥታስሩት ያሳሰራችሁ፣
ብትገድሉት የሚገላችሁ፣
ሀቅ እውነት ካልጠመቃችሁ፣
ሁልዬም የማይለቃችሁ!
ጸጋዬማ ነው ጸጋችን፣
አድምጡን እንንገራችሁ።
ለጸጋዬ ደብተራው
(ለንደን፣ ህዳር 6 ቀን፣ 1998 ዓ. ም.)