የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ ዕርዳታ ማስተባበሪያ ተቋም (OCHA) በዚህ ሳምንት ከግልገል ጊቤ ሦስት ግድብ የሚለቀቅ ውኃ፣ በአካባቢው የሚገኙ አራት ወረዳዎችን ሊጐዳ እንደሚችል አስታወቀ፡፡

የሰብዓዊ ዕርዳታ ማስተባበሪያ ድርጅቱ እንደገለጸው የኃይል ማመንጫ ጣቢያው አስተዳደር ከመስከረም 19 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ለአንድ ሳምንት ወይም ከዚያ በላይ የሚለቀው ውኃ በአካባቢው የሚገኙ በዳሰነች፣ በኛንጋቶም፣ በሐመርና በሰላማጐ ወረዳዎች የሚገኙ መሠረተ ልማቶችንና ማኅበረሰቡን ሊጎዳ እንደሚችል አስታውቋል፡፡

ብሔራዊ የአደጋና ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን የሚለቀቀው ውኃ የሚያስከትለው የጐርፍ አደጋ ከክልሎች በሚቀርብለት የአስቸኳይ ዕርዳታ ጥያቄ ፈጣን ምላሽ እንደሚሰጥ ታውቋል፡፡ በኤልኒኖ ሳቢያ በተከሰተው ድርቅ ከብቶቻቸውንና ጥሪታቸውን ያጡ ነዋሪዎች ቢያንስ በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት የባሰ ድህነትና ዕዳ ውስጥ ሊዘፈቁ እንደሚችሉ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ ዕርዳታ ጽሕፈት ቤት ገልጿል፡፡

የሰብዓዊ ዕርዳታ ጽሕፈት ቤቱ የዩኤስኤአይዲ ጥናትን ዋቢ በማድረግ እንደገለጸው፣ ከድርቁ በመቀጠል ጐርፍ ካደረሰባቸው ጉዳት ለመውጣት በትግራይና በደቡብ የሚገኙ ነዋሪዎች የቀሯቸውን ከብቶች ወደ መሸጥና የተለያዩ የብድር አማራጮችን ሊጠቀሙ እንደሚችሉ ከድምዳሜ ላይ ደርሷል፡፡ በመሆኑም አስቸኳይ የሰብዓዊ ዕርዳታ ካልተገኘ በሴፍቲኔት የታቀፉ ነዋሪዎች ዕዳ 60 በመቶ፣ እንዲሁም በሴፍቲኔት ባልታቀፉ አካባቢዎች ዕዳቸው በ57 በመቶ ሊጨምር እንደሚችል ጠቁሟል፡፡

በተለይ በምሥራቅ ደቡብ ትግራይ አካባቢዎች የተረጂዎች ዕዳ ለሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት እስከ 301 ዶላር በቤተሰብ ሊሆን እንደሚችል ገምቷል፡፡

በአገሪቱ ትምህርት ቤቶች ሲከፈቱ የአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት ፈጣን ምላሽ የሚሰጥ አደረጃጀት ሊፈጠር እንደሚገባ ምክረ ሐሳብ አቅርቧል፡፡