ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን ለማስከበርና የሕዝብና የዜጎችን ሰላምና ፀጥታ ለማስጠበቅ የሚኒስትሮች ምክር ቤት መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የደነገገ ሲሆን፣ በቅርቡ በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች የተስተዋለውን የፀጥታ መደፍረስ በአጭር ጊዜ ውስጥ በቁጥጥር ሥር አድርጎ የሕዝቡን ሰላምና ፀጥታ ወደ ነበረበት ለመመለስ በየቦታው ለታየው ሁከት፣ ረብሻና ሥርዓት አልበኝነት ዋንኛ መገለጫ በሆኑ አውዳሚ ተግባራት ላይ የተጣለውን ክልከላ እንዲሁም ክልከላዎቹ ሲጣሱ በአዋጁ መሠረት የሚወስዱ የአስቸኳይ ጊዜ ዕርምጃዎችን በመለየት አስቀድሞ ለሕዝብ ማሳወቅ እንዲሁም አዋጁ ተፈጻሚ ሆኖ በሚቆይበት ጊዜ ክልከላዎቹን ጥሰው በሚገኙ ሰዎችና ድርጅቶች ላይ ተገቢውን የአስቸኳይ ጊዜ ዕርምጃ መውሰድ ተገቢ ሆኖ ስለተገኘ የሕዝብን ሰላምና ፀጥታ ለማስጠበቅ የወጣው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ቁጥር———-መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. አንቀፅ 13/2/ እና በደንቡ አንቀጽ 4 በተፈቀደው መሠረት የሚከተለው መመርያ ወጥቷል።


ክፍል አንድ

የተከለከሉ ተግባራት

ንዑስ ክፍል አንድ

በማንኛውም የአገሪቱ ክፍሎች የተከለከሉ ተግባራት

አንቀጽ1. ሁከትና ብጥብጥ የሚያስነሳ ቅስቀሳና ግንኙነት ማድረግ

  • ማንኛውም ሁከት፣ ብጥብጥና በሕዝቦች መካከል መጠራጠርና መቃቃር የሚፈጥር፣ ይፋዊም ሆነ ድብቅ ቅስቀሳ በማናቸውም መልኩና ዘዴ ማድረግ፣ ጽሑፍ ማዘጋጀት፣ ማተምና ማሰራጨት፣ ትዕይንት ማሳየት፣ በምልክት መግለጽ ወይም መልዕክትን በማናቸውም ሌላ መንገድ ለሕዝብ ይፋ ማድረግ፣ ፍቃድ ሳይኖር ማንኛውንም ኅትመት ወደ አገር ውሰጥ ማሰገባት ወይም ወደ ውጪ አገር መላክ፤
  • መልዕክት በኢንተርኔት፣ በሞባይል፣ በጽሑፍ፣ በቴሌቪዥን፣ በሬዲዮ፣ በማኅበራዊ ሚድያ ወይም ሌሎች የግንኙነት ዘዴዎች መለዋወጥ።

አንቀጽ 2

ከሽብርተኛ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ማድረግ

  • በሽብር ከተሰየሙ ድርጅቶችና ከፀረ ሰላም ቡድኖች ጋር ማናቸውንም ግንኙነት ማድረግ፣
  • የአሽባሪ ድርጅቶችን የተለያዩ ጽሑፎች መያዝ ማሰራጨት፣ ዓርማቸውን መያዝ ወይም ማስተዋወቅ፣
  • የቴሌቪዥን ወይም የሬድዮ ፕሮግራምን መከታተል፣ የኢሳት፣ የኦ.ኤም.ኤን. እና የመሳሰሉትን የሽብርተኛ ድርጅቶች ሚዲያዎችን ማሳየት፣ መከታተልና ሪፖርት ማድረግ የተከለከለ ነው።

አንቀጽ 3

ያልተፈቀደ ሠልፍና የአደባባይ ስብሰባ

የሕዝብና የዜጎች ሰላምና ፀጥታ ለማስጠበቅ ሲባል ከኮማንድ ፓስቱ ፈቃድ ውጭ ማናቸውም ሠልፍና የአደባባይ ስብሰባ ማድረግ የተከለከለ ነው።

አንቀጽ 4

ለሕዝብ አገልግሎት አለመስጠት

  1. ሕዝብ የሚጠቀምባቸውን ወይም ፈቃድ የወጣባቸው የንግድ ሥራዎች፣ ሱቆች ወይም የመንግሥት ተቋማት መዝጋት ወይም ምርትና አገልግሎት ማቋረጥ፣ ከሥራ ቦታ ያለ በቂ ምክንያት መጥፋት ወይም ሥራ ማቆም፣ ተገቢውን አገልግሎት አለመስጠት፣ ሥራን መበደል፣
  2. የመንግሥት ወይም የግል ተቋማት ሠራተኞች ወደ መደበኛ ሥራቸው እንዳይገቡ መዛትና ማስፈራራት የተከለከለ ነው።

አንቀጽ 5

በትምህርት ተቋማት አድማ ማድረግ

በትምህርት ቤቶች፣ በዩኒቨርስቲዎችና በሌሎች የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የመማር ማስተማር ሒደትን የሚያውክ አድማ ማድረግ፣ የትምህርት ተቋማትን መዝጋት ወይም በነዚህ ተቋማት ላይ ጉዳት ማድረግ የተከለከለ ነው።

አንቀጽ 6

በስፖርት ማዘውተሪያዎች አድማ ማድረግ

በስፖርት ማዘውተሪያ ማዕከላት ከስፖርታዊ ጨዋነት ውጪ የሆኑ ሁከቶችን፣ ብጥብጦችን መፍጠር የተከለከለ ነው።

አንቀጽ 7

የተሽከርካሪዎችን እንቅስቃሴ ማወክ

የተሽከርካሪ፣ የእግረኛና ሌሎች የመጓጓዣ ዘዴዎችን እንቅስቃሴ መንገድ በመዝጋት በዛቻና በሌሎች መሰል ድርጊቶች ሰላማዊ እንቅሰቃሴን ማወክ፣ አገልግሎት ማስተጓጎል፣ የመጓጓዣ ዋጋ ታሪፍ መጨመር፣ የሚመለከተው አካል ከደለደለው የሥራ ሥምሪት ውጪ መሆን የተከለከለ ነው።

አንቀጽ 8

በመሠረተ ልማቶችና ሃይማኖታዊ ተቋማት ላይ ጉዳት ማድረስ

በግል፣ በሕዝብና በመንግሥት ማናቸውም ተቋማት፣ በመሠረተ ልማት፣ በኢንቨስትመንትና በሌሎች የልማት አውታሮች እንዲሁም በሃይማኖታዊ ተቋማት ላይ በማንኛውም መንገድ ጉዳት ማድረስ ወይም ዘረፋ መፈጸም የተከለከለ ነው።

አንቀጽ 9

ሕዝባዊና ብሔራዊ በዓላትን ማወክ

ሕዝባዊና ብሔራዊ በዓላትን በማንኛውም ሁኔታ ማወክ፣ ማደናቀፍ ወይም ከበዓሉ ዓላማ ጋር የማይገናኙ የፖለቲካ አጀንዳዎች ወይም መፈክሮችን በማንኛውም መንገድ ማስተጋባት የተከለከለ ነው።

አንቀጽ 10

ሃይማኖታዊ፣ ባህላዊና ሕዝባዊ በዓላት ላይ ቅስቀሳ ማድረግ

ሃይማኖታዊ ተቋማት ውስጥ በሚደረጉ ስብከቶችና ትምህርቶች ሃይማኖታዊ አስተምህሮት ከማድረግ ውጪ በሕዝቦች መካከል መጠራጠርና መቃቃርን የሚፈጥር፣ በኅብረተሰቡ ላይ ሥጋት የሚፈጥር፣ ሁከትና ብጥብጥ የሚቀሰቅስ ቅስቀሳ ማድረግ የተከለከለ ነው።

አንቀጽ 11

የሕግ አስከባሪዎችን ሥራ ማወክ

  • የሕግ አስከባሪ አካላት የሚሰጡትን ማንኛውም ትዕዛዝ አለማክበር ስራቸውን ማደናቀፍ፣ ለፍተሻ አለመተባበር ወይም እንዲቆም ሲጠየቅ አለማቆም፣ ኬላዎችን ጥሶ ማለፍ የተከለከለ ነው፣
  • በሕግ አስከባሪ አካላት ባልደረቦች ላይ ጥቃት መፈጸም ወይም ለመፈጸም መሞከር የተከለከለ ነው፣

አንቀጽ 12

ያልተፈቀዱ አልባሳት መልበስ

የሕግ አስከባሪ ኃይሎችን ዩኒፎርም መልበስ፣ ይዞ መገኘት፣ በቤት ማስቀመጥ፣ አሳልፎ መስጠትና መሸጥ ክልክል ነው።

አንቀጽ 13

የጦር መሣሪያ ይዞ መግባት

ማናቸውም የጦር መሣሪያ፣ ስለት ወይም እሳት የሚያስነሱ ነገሮችን ወደ ገበያ፣ ሃይማኖት ተቋማት፣ ሕዝባዊ በአላት የሚከበሩበት ወይም ወደ ማናቸውም ሕዝብ የሚሰበሰብበት ቦታ ይዞ መግባት የተከለከለ ነው።

አንቀጽ 14

ትጥቅን በሦስተኛ ሰው እጅ እንዲገባ ማድረግ

ማንኛውም የሕግ አስከባሪ አካላት ባልደረባ ወይም ማንኛውም ሕጋዊ ትጥቅ ያለው ሰው ትጥቁን በማንኛውም ሁኔታ በሦስተኛ ሰው እጅ እንዲገባ ማድረግ ክልክል ነው።

አንቀጽ 15

መቻቻልንና አንድነትን የሚጎዳ ተግባር መፈጸም

ማንነትን ወይም ዘርን መሠረት ያደረገ ማንኛውም ዓይነት ጥቃት መፈጸም ወይም ጥቃት እንዲፈጸም የሚያነሳሳ ንግግር መናገር የተከለከለ ነው።

አንቀጽ 16

የአገርን ሉዓላዊነት፣ ደኅንነት፣ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓት የሚጎዳ ተግባር መፈጸም

  • ማንኛውም ሰው ከውጭ መንግሥታትም ሆነ ከውጭ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ጋር የአገር ሉዓላዊነት፣ ደኅንነትና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓትን ሊጎዳ የሚችል ግንኙነትና የመልዕክት ልውውጥ ማድረግ የተከለከለ ነው፡፡
  • ማንኛውም የፖለቲካ ፓርቲ የአገርን ሉዓላዊነት፣ ደኅንነትና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን ማናቸውም ጋዜጣዊ መግለጫ ለአገር ውስጥም ሆነ ለውጭ ሚዲያዎች መስጠት ክልክል ነው።

አንቀጽ 17

ያልተፈቀደ ቦታ መገኘት

ከስደተኛ ካምፕ አግባብ ካለው አካል ከሚሰጥ ፈቃድ ውጭ መውጣት ወይም ሕጋዊ ቪዛ ሳይኖረው ወደ አገር ውስጥ መግባት የተከለከለ ነው።

አንቀጽ 18

ያለፈቃድ ስለሚደረግ የዲፕሎማቶች እንቅስቃሴ

የኮማንድ ፖስቱ ዕውቅናና ፈቃድ ሳያገኙ ዲፕሎማቶች ለራሳቸው ደኅንነት ጥበቃ ሲባል ከአዲስ አበባ ከአርባ (40) ኪሎ ሜትር ራዲየስ ውጪ መንቀሳቀስ የተከለከለ ነው።

አንቀጽ 19

የሕግ አስከባሪ አካላት ግዳጅ ላይ ስለመገኘት

ማንኛውም የሕግ አስከባሪ አካል ባልደረባ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተፈጻሚ በሚሆንበት ጊዜ ከሥራ መልቀቅ ወይም አስገዳጅ ሁኔታ ካልተፈጠረ በስተቀር የዓመት ዕረፍት ፍቃድ መውሰድ ክልክል ነው።

አንቀጽ 20

የሕዝብን ሰላምና ፀጥታ ለማደፍረስ ድጋፍ ማድረግ

በዚህ መመርያ የተከለከሉ ተግባራትን በመተላለፍ ሕገወጥ ድርጊት የሚፈጽሙ ሰዎችን፣ በገንዘብና በቁሳቁስ ወይም በማናቸውም ሌላ መንገድ መደገፍ እንዲሁም ከለላ መስጠት፣ መደለያ መስጠት፣ ማበረታታት የተከለከለ ነው።

ንዑስ ክፍል ሁለት

በተወሰኑ የአገሪቱ አካባቢዎች እንዳይፈጸሙ የተከለከለ ተግባራት

ከላይ በንዑስ ክፍል አንድ የተደነገነገው እንደተጠበቀ ሆኖ ከአንቀጽ 21-24 የተዘረዘሩት ክልከላዎች ኮማንድ ፖስቱ እየወሰነ ይፋ በሚያደረጋቸው ቦታዎች ወይም አካባቢዎች ላይ ተፈጻሚ ይሆናሉ።

አንቀጽ 21

የጦር መሣሪያ ይዞ መንቀሳቀስ

ማናቸውም የጦር መሣሪያ፣ ሥለት ወይም እሳት የሚያስነሱ ነገሮችን ከግቢውና ይዞታው ውጪ ይዞ መንቀሳቀስ የተከለከለ ነው።

አንቀጽ 22

በልማት አውታሮችና መሠረተ ልማቶች ላይ የሚሰነዘር ጥቃት

የኢኮኖሚ አውታሮች፣ መሠረት ልማትና የኢንቨስትመንት ተቋማት፣ የእርሻ ልማቶች፣ በፋብሪካዎችና በመሰል ተቋማት አካባቢ ከቀኑ 12 ሰዓት በኋላ እስከ ንጋት 12 ሰዓት ድረስ ከተፈቀደለት ሠራተኛ በስተቀር ማንኛውም ሌላ ሰው መንቀሳቀስ የተከለከለ ነው፣ ከላይ በተመለከቱት ቦታዎች የሰዓት እላፊውን ተላልፎ በተገኘ ማንኛውም ሰው ላይ የጥበቃ ወይም የሕግ አስከባሪ አካላት አስፈላጊውን ዕርምጃ እንዲወስዱ ሥልጣን ተሰጥቷቸዋል።

ክፍል ሁለት

የተከለከሉ ተግባራት ተፈጽሞ ሲገኝ ስለሚወሰዱ የአስቸኳይ ጊዜ ዕርምጃዎች

አንቀጽ 27

ዕርምጃ ለመውሰድ ሥልጣን ስላለው ሰው

ከላይ በክፍል አንድ ከአንቀጽ 1 እስከ 24 የተመለከቱ የተከለከሉ ተግባራትን ፈጽመው በተገኙ ሰዎችና ድርጅቶች ላይ የሕግ አስከባሪዎችና ባልደረቦቻቸው በአዋጁና በዚህ መመርያ የተዘረዘሩ የሚከተሉትን የአስቸኳይ ጊዜ ዕርምጃዎችን ሊወስዱ ይችላሉ፡፡

አንቀጽ 28

ክልከላዎች ሲጣሱ ስለሚወሰዱ ዕርምጃዎች

ከላይ በክፍል አንድ የተመለከቱ ክልከላዎችን ተላልፈው በተገኘ ማንኛውም ሰው ላይ የሕግ አስከባሪዎች፣

  1. ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ በቁጥጥር ሥር ማዋል፣
  2. አዋጁ ተፈጻሚነቱ እስከሚያበቃበት ጊዜ ድረስ ኮማንድ ፖስቱ በሚወስነው ቦታ እንዲቆይ ማድረግ፣
  3. ተገቢውን የተሃድሶ ትምህርት በመስጠት የሚለቀቀውን እንዲለቀቅ ወደ ፍርድ ቤት የሚቀርበውን ደግሞ እንዲቀርብ ማድረግ፣
  4. ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ በማናቸውም ሰዓት ብርበራ ለማድረግ የአካባቢውን ሕዝብና ፖሊስ  በማሳተፍ ማንኛውንም ወንጀል የተፈጸመበት ወይም ሊፈጸምበት የሚችል ንብረት መያዝ  ወይም ንብረቱ ባለበት እንዲጠበቅ ማድረግ፣
  5. በማንኛውም ሬድዮ፣ ቴሌቪዥን፣ ጽሑፍ፣ ምሥል፣  ፎቶ ግራፍ፣  ቲያትርና ፊልም የሚተላለፉ መልዕክቶችን መቆጣጠርና መገደብ፣
  6. የተዘረፉ ንብረቶችን ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ በመፈተሽ ለባለቤቶቹ እንዲመለሱ ማድረግ፣
  7. በትምህርት ተቋማት ሁከትና ረብሻ ተሳትፎ በሚያደርጉ ተማሪዎችና ሠራተኞች ላይ  ሕጋዊ ዕርምት መውሰድ አስተዳደራዊ ዕርምጃ እንዲወሰድ ለተቋማቱ ትዕዛዝ መስጠት፣
  8. ማንኛውም የሕዝብን ሰላምና ፀጥታን ሊያደፈርሱ ይችላሉ ወይም ለጉዳት ተጋላጭ ይሆናሉ ተብለው የሚጠረጠሩና የሚታሰቡ ሰዎችን ወይም ቡድኖችን ወደ ተወሰነ አካባቢ እንዳይገቡ እንዳይገኙ ወይም በተወሰነ አካባቢ ብቻ እንዲቆዩ ማድረግ እና
  9. አግባብነት ያላቸውን ዕርምጃዎችን መውሰድ ይችላል፡፡

አንቀጽ 23

ስለ ሰዓት እላፊ

ማናቸውም ሰው በኮማንድ ፖስቱ ውሳኔ የሰዓት እላፊ በይፋ በሚገለጽበት ቦታና ጊዜ የሰዓት እላፊ ክልከላን በመተላለፍ ከቦታ ቦታ መንቀሳቀስ አይፈቀድም፡፡

አንቀጽ 24

ሁከትን ለማስቆምና አደጋን ለመከላከል የሚደረግን እንቅስቃሴ ማወክ

ሰላምና ፀጥታን ሊያደፈርሱ ይችላሉ ተብለው የሚጠረጠሩ ሰዎች ወይም ቡድኖችን ወይም ለጉዳት ተጋላጭ ናቸው ተብለው የሚገመቱ ሰዎች ወይም ቡድኖች ወደ ተወሰነ አካባቢ ወይም ሕንፃ እንዳይገቡ ወይም በተፈቀደላቸው አንድ የተወሰነ አካባቢ ብቻ እንዲቆዩ የተሰጠውን ትዕዛዝ መተላለፍ ክልክል ነው፡፡ ለአካባቢው ደኅንነት አስፈላጊ መሆኑ ታምኖበት ወደ ተዘጋ መንገድ ማንም ሰው እንዳይገባ ኮማንድ ፖስቱ የሰጠውን ዕግድ ወይም ክልከላ መተላለፍ ክልክል ነው፡፡

ንዑስ ክፍል ሦስት

መረጃ የመስጠትና የማስታወቅ ግዴታ

አንቀጽ 25

የተከራይ መረጃ የመያዝና የመስጠት ግዴታ

ማንኛውም ቤት፣ ቦታ፣ ክፍል ወይም ተሽከርካሪ ወይም ተመሳሳይ መገልገያ አከራይ የሆነ ሰው የተከራዩን ማንነት በዝርዝርና በጹሑፍ የመያዝና በአቅራቢያው ላለ ፖሊስ ጣቢያ በ24 ሰዓት ውስጥ የማሳወቅ ግዴታ አለበት፡፡ በተጨማሪም የውጭ አገር ዜጋን ያከራየ እንደሆነ የፓስፖርቱን ኮፒና የኪራዩን ውል በአቅራቢያው ላለ ፖሊስ ጣቢያ የማሳወቅ ግዴታ አለበት፡፡

አንቀጽ 26

መረጃ የመስጠት ግዴታ

የሕዝብ ሰላምና ፀጥታ ለማስጠበቅ ሲባል ማንኛውም ተቋም መረጃ እንዲሰጥ በየደረጃው ባለ የሕግ አስከባሪ አካል ሲጠየቅ የመስጠትና የመተባበር ግዴታ አለበት።

አንቀጽ 29

ራስን ለመከላከል በሕግ አስከባሪዎች ስለሚወሰድ ዕርምጃ

ሕግ አስከባሪዎችናቀ በድርጅቶች ጥበቃ ሥራ ላይ የተሰማሩ ሰዎች ከላይ የተመለከቱትን ክልከላዎች እንዲሁም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ለማስፈጸም በሚያደርጉት እንቅስቃሴ በጦር መሣሪያ ወይም በስለትና ሕይወታቸውንና ንብረታቸውን አደጋ ላይ የሚጥል ጥቃት በተሰነዘረባቸው ጊዜ ራሳቸውን ለመከላከል የሚያስችላቸውን ዕርምጃ ሊወስዱ ይችላሉ፡፡

አንቀጽ 30

በትምህርት ተቋማት የመግባት ሥልጣን

በትምህርት ቤቶች፣ በዩኒቨርስቲዎችና በሌሎች የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ አድማ የሚያደርጉ ሰዎችን ለመያዝና ችግሩን ለማስቆም የሕግ አስከባሪ አካላት በእነዚህ ተቋማት ውስጥ በመግባት አስፈላጊውን ዕርምጃ ለመውሰድ ይችላሉ፣ እንዲሁም በሌሎች የግልና የመንግሥት ተቋማት ውስጥ አድማ የሚያድርጉ ሰዎችን ለመያዝና ሰላምና ፀጥታ ለማረጋገጥ የሕግ አስከባሪ አካላት ባልደረቦች በእነዚህ ተቋማት ውስጥ ለመግባት እንዲሁም አስፈላጊ ከሆነ ሊቆዩ ይችላሉ፡፡

ክፍል ሶስት

ተሃድሶና ፍርድ ቤት ስለማቅረብ

አንቀጽ 31

በሕግ መሠረት በኮማንድ ፖስቱ የሚደረግ የተሃድሶ ዕርምጃዎች

  1. ለፍርድ መቅረብ ያለበትን ፍርድ ቤት እንዲቀርብ ያደርጋል
  2. ባለፈው አንድ ዓመት ውስጥ በተፈጸሙ ሁከትና የብጥብጥ እንቅስቃሴዎች ላይ በቡድን ወይም በግል የተሳተፈና

ሀ) የጦር መሣሪያ ወይም ማንኛውንም የግልም ሆነ የመንግሥት ንብረት የዘረፈና በአቅራቢያው ለሚገኝ የሕግ አስከባሪ ኃይል የዘረፈውን መሣሪያና ንብረት ይህ መመርያ ከወጣ ጊዜ ጀምሮ በአሥር ቀናት ውስጥ በአቅራቢያው  ላለ ፖሊስ ጣቢያ የመለሰና እጁን የሰጠ ሰው፣

ለ) ከዚህ በፊት ለሕገወጥ ተግባራት የገንዘብና ቁሳቁስ ድጋፍ ያደረገና ይህ መመሪያ በወጣ በአሥር ቀናት ውስጥ ለፖሊስ ጣቢያ እጁን የሰጠ ሰው፣

ሐ) ወረቀት በመበተን ፣ አድማ በማድረግ የተሳተፈ፣ ያነሳሳ ሰው ይህ መመርያ በወጣ አሥር ቀናት ውስጥ ለፖሊስ ጣቢያ እጁን የሰጠ ሰው፣

መ) ሰው የገደለ፣ ማንኛውንም ንብረት ያቃጠለ፣ ማንኛውንም ወንጀል የፈጸመ ይህ መመሪያ ከወጣበት ጊዜ ጀምሮ በአሥር ቀናት ውስጥ ለፖሊስ ጣቢያ እጁን የሰጠ  ሰው፣ እንደ የወንጀል ተሳትፎው ቀላልና ከባድነት፣ ዋና ፈጻሚና አባሪ ተባባሪ መሆኑ ታይቶ በኮማንድ ፖስቱ የተሃድሶ ትምህርት ተሰጥቶት እንዲለቀቅ ይደረጋል፡፡

Leave a Reply