Girma-Siefu.jpg

 

 

 

 

 

 

 

 

 

ታሪከኛው የ2007 ምርጫ ተጠናቆ ገዢው ፓርቲ `መንግሰት` መስርቻለሁ ባለ ማግስት በተጀመረ ህዝባዊ እንቅስቃሴ ሲናወጥ የከረመው መንግስት የሁለተኛ ዓመት ስራውን ለመጀመር ማሟሻ ንግግር የሚያደርጉት ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ መሰከረም 30/2009 ንግግር አድርገዋል፡፡ ተከትሎም የግንባሩ ልሣን ፋና ብሮድካሰቲንግ ማስመሰያ ውይይት አዘጋጅቷል፡፡ ከፕሬዝዳንቱ ሪፖርት እና ከፋና ውይይት ምን እንጠብቅ የሚል ጥያቄ ለራሴ አቅርቤ ትዝብቴን አሰቀምጫለሁ፡፡ የፕሬዝዳንቱ የመክፈቻ ንግግር እና የፋና የውይየትት ፕሮግራም በተለመደው መስመር ማዘናጋት እና አሁንም ገዢው ፓርቲ ህወሃት/ኢህአዴግ መሆኑን አረጋግጦ ማለፍ ነው፡፡ የተወሰኑ ነጥቦችን አንስተን ለመመልከት እንሞክር፡፡

እንደ መነሻም በሰሞኑ ለነበረው የህዝባዊ እንቅስቃሴ ሞተር ለነበረው ወጣት ትውልድ ማዘናጊያ የሚሆን 10 ቢሊዮን ብር መመደቡን አብሰረዋል የዚህ ዓመት በጀት ጉዳይ በሰኔ 30 መጠናቀቁን የሚያስታውስ ሰው ያለ አልመሰላቸውም፡፡ ቀደም ሲል የኦሮሚያ ፕሬዝዳንት የነበሩት አቶ ሙክታርም ለኦሮሚያ ቀወስ 3 ቢሊዮን በጀት ዓመቱ ሊጠናቀቅ ሶሰት ወር ሲቀረው ለወጣቱ ሰራ ፈጠራ መድነበናል ብለው ነበር፡፡ ይህ በጀት የኦሮሚያን ችግርም አላበረደም አቶ ሙክታርንም በስልጣን ሊያቆይ አልቻለም፡፡ 10 ቢሊዮን ብር በጀት የወጣቱን ጥያቄ ለመመለስ የወሰዱትን እርምጃ በአስገራሚነቱ ተወዳዳሪ ሊኖረው አይችልም፡፡ ምን ማለት ነው “ወያኔ ይውደም!!” ብሎ መፈክር ለሚያሰማ ወጣት መልሱ “አርፈህ ወደ ስራ ግባ!!” እንደማለት ነው፡፡ ወጣቱ የጠየቀው የስርዓት ለውጥ ነው፡፡ የስርዓት ለውጥ የሚያመጣውን ማነኛውንም እድል የስራ ዕድልን ጨምሮ ለማየት ይፈልጋል፡፡ 25 ዓመት ተሞክሮ ያልተሳካለት አብዮታዊ ዲሞክራሲ ትንተና መልስ እንደማይሰጠው ነው ወጣቱ የተናገረው፡፡ ለዚህ መልስ መስጫው መንገድ ተዘዋዋሪ የብድር ገንዘብ ተዘጋጅቶዋል የሚል ፌዝ ያዘለ መልስ ያስቃል፡፡ ህወሃት/ኢህአዴግ ጉዳዩን የምር እንዳልያዙት የሚያስታውቀው በቅርቡ ሬዲዮ ፋና በጠራው ስብሰባ ላይ የተጋበዙት የወጣቶች ተወካይ የኢህአዴግ አደረጃጀት ወጣት ናቸው፡፡ እነዚህ ወጣቶች ሰልፍ አልወጡም ጥያቄም አላቀረቡም፡፡ ይልቁንም ጥያቄ ያነሱትን ወጣቶች ፀረ-ሰላም እያሉ የሚከሱ ቡድን ተወካይ ናቸው፡፡ ምን አልባትም የተመደበው በጀት ለዚህ ቡድን ሊያገለግል ይችላል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ከአንድ ጓደኛዬ ጋር ስናወራ ይህ የስርዓቱ ትክክለኛ መገለጫ ነው፣ ችግሮች የሚፈቱት በገንዘብ ይመስላቸዋል፡፡ ሙሰኛ ስርዓት ህዝብንም ሙሰኛ አድርጎ በማየት በገንዘብ ለመደለል ይሞክራል ነው ያለኝ፡፡ እኔም ተሰማምቼበታለሁ፡፡ ገንዘብ ካለ በሰማይ መንገድ አለ ከሚል የዘራፊዎች ቡድን ከዚህ የተሻለ የመፍትሔ አቅጣጫ አይገኝም፡፡ የወጣቱ ጥያቄ የስርዓት ለውጥ ነው፡፡ መልሱም እንዴት በተረጋጋ ሁኔታ የስርዓት ለውጥ እናምጣ የሚለው ነው፡፡ መልሱን ከወጣቱ ጋር በግልጽ መወያየት ነው፡፡ ወጣቱ ተወካይ የለውም እንዳትሉን ከዚህ በፊት እንደዳልኩት እኔ ዞን ዘጠኝ የሚባሉትን ወጣቶች ወክያለሁ ……. ሌላም መጨመር ይቻላል፡፡ ከፎረም ውጭ ……

በፕሬዝዳንቱ ንግግር ውስጥ ትኩረት አግኝቶ በተለያየ መንገድም ትኩረት የሳባው የምርጫ ህግ ማሻሻል የሚመለከተው ነው፡፡ የምርጫ ህግ ማሻሻል ሲባል ብዙ ሰው “ህገ መንግሰት ማሻሻል” መሆኑንም ዘንግቶታል፡፡ ከብዙዎቹ አንዱ ፕሬዝዳንት ሙላቱ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ህገ መንግሰት አንቀፅ 54/2 በአንድ ምርጫ ክልል አብላጫ ድምፅ ያገኘ ያሸንፋል በሚለው መስረት ይመረጣል ነው የሚለው፡፡ ሰለዚህ ሌላ የምርጫ ስርዓት ማድረግ አይቻልም፡፡ ህገ መንግሰቱ ሳይሻሻል ማለት ነው፡፡ ሌላው ህወሃት/ኢህአዴግ ማስተላለፍ የፈለገውን መልዕክት ብዙ ሰው የተቀበለው ይመስለኛል፡፡ ይህ መልዕክት “ህውሃት/ኢህአዴግ እና አጋሮች አሸንፈዋል” የሚለው ነው፡፡  ይህ ማለት ግን “ሁሉም ሰው መርጦናል ማለት አይደለም” የሚለውን መልዕክት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ምርጫው ነፃ፣ ፍትሃዊና ታማኝነት ነበረው ለማለት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚያስፈልገው ነፃ፣ ፍትሃዊ፣ ግልፅነት ያለው ምርጫ እንጂ የምርጫ ስርዓት ለውጥ አይደለም፡፡ የምርጫ ስርዓት ለውጥ የሚጠቅመው በቢሮ ቁጭ ብለው የፓርቲ ሰርተፊኬት እና ማህተም በፌስታል ይዘው የብሄር ተወካይ ነን በሚል የውክልና ስልጣን ለማግኘት ለሚፈልጉ ጥቂት ግለሰቦች ነው፡፡ አሁን ባለው ምርጫ ስርዓት ኢትዮጵያ ውስጥ የብዙሃን ፓርቲ ስርዓትን ማረጋገጥ ይቻላል፡፡ ከዚህ የተለይ የምርጫ ህግ የሚመክሩን የውጭ አማካሪዎችም ሆኑ ኢትዮጵያዊያን ልሂቃን በኢህአዴግ ምርጫ አሸንፊያለሁ ችግሩ የምርጫ ስርዓቱ ነው በሚለው መታለላቸውን ማስታወስ ይኖርብኛል፡፡ በመደራጅት መብት ስም ማንም ሱሰኛ የፓርቲ ሰርተፊኬት ይዞ ዕጩ የሀገር መሪ ቡድን ነኝ ሲል ዝም ሊባል አይገባም፡፡ በምርጫ ስርዓት ማሻሻል ሰምም የህዝብ ውክልና ማገኘት ዕድል ሊመቻች አይገባም፡፡

በኢትዮጵያ ሀገራችን ውይይት አጅግ በጣም አስፈላጊ እና በእጅጉ የጎደለን የሰልጣኔ መንገድ እንደሆነ ይስማኛል፡፡ ውይይት ሲባል ደግሞ ገዢዎች ንግግር ሲያደርጉ የሚያዳምጣቸውን የፎረም ተወካዮች ሰብሰቦ ሲሞጋገሱ መዋያም መድረክ አይደለም፡፡ ውይይት ሲባል ሃሳብ ተለዋውጦ የሃሳብ ሽግሽግ ለማድረግ መዘጋጀትንም ይጠይቀል፡፡ የሃሳብ ሽግሽግ የሚደረግበት የውይይት መድረክ ሀገራችን በእጅጉ ያስፈጋታል፡፡ በሰብሰባ ውስጥ የህዝብ ሰሜት የሚኮረክሩ ንግግሮች ከተደረጉ በኋላ ሹሞች ያሻቸውን በማጠቃለያነት ተናግረው፣ ሲፈልጉም ዘለፋ አክለውበት ምን ታመጣላችሁ፣ ከቻላችሁ ተደራጅታችሁ እራሳቸሁን አጠናክራችሁ መጥታችሁ ግጠሙን በሚል ፉከራ የሚጠናቀቅ መሆን የለበትም፡፡ ይህ ዓይነቱ መድረክ የውይይት ሳይሆን የፉከራና ቀረርቶ ነው ሊባል የሚችለው፡፡ ተጠናክሮ መጥቶ ለመጋጠም የሕወሃት/ኢህአዴግ ምክር አስፈላጊ አይመስለኝም፡፡ መጋጠሚያ ቦታውን እና የመጋጠሚያ ህጉን ማስተካክል ነው፡፡ የብረት ቦክስ ይዞ ሜዳ እየገቡ ባዶ እጅ ያለን ተጋጣሚ ማድማትና ማቁሰል ጉብዝና ሳይሆን ህገወጥ መሆን እና ውንብድና ነው፡፡

ሌላው የሪፖርቱ አስገራሚ ነጥብ የዜጎች መፈናቀል የሚመለከተው ነው፡፡ ዜጎችን ማፈናቀሉ ትክክል እንዳልሆነ ተገንዝቢያለሁ ያለ የሚመስለው ገዢው ፓርቲና መንግሰት በተዘዋዋሪ ማፈናቀል እቀጥላለሁ ነገር ግን የሚሰጠውን ካሳ ከጊዜው የዋጋ ንረት፣ የምርት ዋጋ እና ምርታማነት እድገት ጋር ተገናዝቦ ይሻሻላል የሚል መግለጫ እየሰጠ ይገኛል፡፡ አታፈናቅሉኝ ያለን ዜጋ ዋጋ ጨምረን እናፈናቅልህ እያሉት ነው፡፡ ህውሃት/ኢህአዴግ ችግሩን ከመስረቱ መፍታት ሳይሆን አሁንም ዙሪያ ጥምጥም መሄድ መርጠዋል፡፡ የህዝቡ ጥያቄ የመሬት ባለቤትነት ጥያቄ መልስ ያግኝ ነው፡፡ የያዘውን መሬት ለልማት ሲባል እንዴት እና በምን ዓይነት ሁኔታ እንደሚለቅ በኋላ የሚደረስበት የውይይት ነጥብ ነው፡፡ ይህ ጉዳይ እንደ ምርጫ ሰርዓቱ ህገ መንግሰታዊ ጉዳይ ነው፡፡ ገዢው ፓርተ የመሬት ነገር በመቃብሬ የሚለውን ነገር ወደ ጎን ትቶ መሬት ለባለመሬቱ ማስተላለፍ ይኖርበታል፡፡ ቀሪውን ስንደርስ የምንጫወታው ይሆናል …… ድልድዩን ሰንደርስ እንሻገራለን እንደሚባለው መሆኑ ነው፡፡

የህወሃት/ኢህአዴግ ጥልቅ ተሃድሶ ፍልስፍና ፈርሶ እስከ መሰራት እንደማይደርስ አቶ አባይ ፀሃዬ ነግረውናል ባይነግሩንም የሚታወቅ ሀቅ ነው፡፡ ፈረሰው ይሁን፣ በአሸዋ ላይ ፓርቲያቸውን መስራት የእነርሱ ምርጫ ነው፣ ይህን ምርጫቸውን የምናከብርላቸው ቢሆንም አሁንም የኢትዮጵያን ህዝብ በካበኔ ሹም ሽር ለመሸንገል ተጨፈኑ እናሞኛችሁ ብሎ ማሰብ መፍትሄ ፍለጋ እና ችግሩን መረዳት ላይ እጅግ ልዮነት እንዳለን ማሳያ ነው፡፡ የኢህአዴግ ካቢኔ ማንንም ይዞ ቢመጣ መስመሩን እስከ አላስተካከለ እና በመድበለ ፓርቲ ስርዓት ውስጥ ቁጥጥር የሚደረግበት ካልሆነ ትርጉም የሌለው ድካም ነው፡፡ ምን አልባትም በራሳቸው ስር ሌላ አኩራፊ ከመጨመር ውጭ የተለየ ፋይዳ አይኖረውም፡፡ አቶ ጁነዲን ሳዶን የመሰለ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ፈላስፋ (በሀገር ውስጥ እያለ) አሁን በግልፅ ምንም ስልጣን አልነበረኝም ስልጣኑ የህወሃት ነው ማለቱን ማስታወስ ያስፈልጋል፡፡ ተራው የማን ነው? መጠበቅ ነው፡፡

በመጨረሻ በቅርቡ ይወጣል የሚባለውን “የኦሮሚያን ልዩ ጥቅም በአዲስ አበባ” የሚመለከት አዋጅ ነው፡፡ ይህ አዋጅ ምን ያህል የተደከመበት ቢሆን ህወሃት/ኢህአዴግ በለመደው መልኩ አዋጅ አድርጎ ካወጣ በኃላ ንትርክ የሚፈጥር እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡ ቢያንስ በቅርቡ ይወጣል ሲባል እንኳን ለህዝብ ለውይይት የሚረዱ አንኳር ነጥቦችን ማጋራት አልቻሉም፡፡ ጉዳዮንም የኦሮሚያ ክልል ብቻ በማድረግ የአዲስ አበባ ነዋሪ ግብር ከፋይ ምንም መረጃ እንዲኖረው እየተደረገ አይደለም፡፡ ሰለዚህ ይህ አዋጅ ምን ይዞ ይመጣል ወደፊት የምናየው ነው፡፡ ፕሬዝዳንቱ ግን በቅርቡ ይታወጃል ብለዋል ….. ቅርብ መቼ ነው? በነገራቸን ላይ ሀረሪ ክልል በሚባለው ውስጥስ ቢሆን ኦሮሚያ ልዩ ጥቅም አያስፈልጋትም ትላላችሁ፡፡ ወይም ክልሉ ለኦሮሚያ ተሰጥቶ የሀረሪ ልዩ ጥቅም የሚባል ነገር በሃሳባችሁ መጥቶ አያውቅም፡፡ እጅግ በቁጥር አነስተኛ የሆኑ ሀረሪዎች ሁልጊዜ አሸናፊ የሚሆኑበት ምርጫ ኢትዮጵያችን ውስጥ ላለው አሳፋሪ የምርጫ አፈፃፀም ጉልዕ ማሳያ ነው፡፡ ሰለምርጫ ከላይ ያነሳሁትን ነጥብ እዚህም ማስታወስ የግድ ይላል፡፡ አዲስ አበባ መቼ ነው በነዋሪዎች ቀጥተኛ ምርጫ ከንቲባ የምትመርጠው የሚል ጥያቄ አሁንም አለኝ፡፡

ይህ ፅሁፍ በምንም መልኩ ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ጋር እንደማይጋጭ እራሴን ሳንሱር አድርጌ ነው የፃፍኩት፣ቢጋጭም ይጋጭ ብዬ ለጥፌዋለሁ፡፡

ቸር ይግጠመን

ምንጭ    _     ዘሃበሻ

Leave a Reply