January 19, 2017

በሚገዛው ሕዝብ ላይ ጦርነት ያወጀ አገዛዝ – ተግባሩን “ስኬት” ሲል ገመገመ

                                                   ግድያ፣ አፈና፣ ቶርቸር፣ ረሃብ፣ የጅምላ ጭፋጨፋ – ስኬት


በቅርቡ ሃይለማርያም ደሳለኝ እንደ እርሱ “አሽከር” ለሚባለው የኢህአዴግ ሸንጎ ንግግር ሲያደርግ ኢህአዴግ የወሰዳቸውና እየወሰደ ያለው እጅግ አረመኔነት የተሞላበት አሠራር የሚደነቀ መሆኑን አስታውቋል። “መቶ በመቶ መርጦኛል፤ እመራዋለሁ” በሚለው ህዝብ ላይ ለታወጀው ክተት አስፈጻሚ መሆኑ፣ ንጹሃንን መጨፍጨፋቸው፣ መታሰራቸው፣ መታፈናቸው፣ ለስቃይ መዳረጋቸው “ስኬት” መሆኑንን ማመልከቱ “የዘመኑ አስገራሚ ትንግርት” እየተባለ ነው።

በአስር ሺህ የሚቆጠሩ ወገኖችን በግፍ አስሮ የሚያሰቃይ አገዛዝ ራሱን በጥንካሬ ሲፈርጅ መስማት አሳዛኝና አሳፋሪ እንደሆነ የሚጠቁሙ እንዳሉት “ግድያ፣ አፈና፣ ማሰቃየት፣ ረሃብ፣ የጅምላ ጭፋጨፋ … ስኬት ተብሎ ሲቀርብ የሚያዳምጥና የሚያጨበጭብ ሸንጎ ህይወት የሌለው በድን ነው” ቢያንስ ለማስመሰል እንኳን የሚከራከር “ሰው” አለመታየቱ የሥርዓቱ የመገልማት ውጤት ነው ሲሉ አስተያየታቸውን የላኩልን ገልጸዋል።

እናት ልጇ አስከሬን ላይ ተቀመጣ በምትገረፍበት፣ ህዝብ በጅምላ በሚጨፈጨፈበት አገር መሪ መሆን አንገት የሚያስደፋ መሆን ሲገባው፣ ደረት ገልብጦ “ዓለም ጠንካራ ናችሁ አለን ማለት የስብዕና መገልማት ነው” ሲሉ ተቃውሞ ያሰሙ ጥቂት አይደሉም።

ድህነትና ረሃብ የሚፈጀውን ህዝብ እየመሩ ማሽካካት ከነተበ አዕምሮ ባለቤቶች የሚሰማ የትዕቢት ጣር ነው” ሲሉ ለጎልጉል አስተያየት የሰጡ እንደሚሉት “ሃይለማርያም የኮሪዶር ወሬና ያደባባይ ዜና መለየት እስኪሳነው ድረስ ታውሯል” ሲሉ ይነቅፉታል። ኢህአዴጎችን ልክ እንደ መንደር ቡድን ኳስ ተጫዋቾች የመሰሏቸው አስተያየት ሰጪ፣ “ህጻናት የበረኪና ዋንጫ ከወሰዱ በኋላ ‘ወንዳታ’ እየተባባሉ እንደሚሞከሻሹት ሁሉ፣ ኢህአዴጎችም ‘ጠንካራ ተባልን ብራቮ፣ ወንዳታ፣ ጫር …’ እየተባባሉ የሚማማሉ በደምና በዝርፊያ የሰከሩ፣ እስከ አፍንጫው የታጠቁ የተሰበሰቡበት የባንዳዎችና የተላላኪዎች ማኅበር ነው” ብለዋል፡፡

እኒሁ ክፍሎች ሰሞኑንን ራሳቸው የሰየሟቸውን የሃይማኖት “አባቶች” ስብስበው ያስተላለፉት የሰላም ጥሪ አሁንም ካላቸው የታወረ አስተሳሰብ የሚመነጭ ማታለል እንደሆነ ተጠቁሟል። የሃይማኖት አስተዳዳሪዎችን ሰብስቦ የመክፈቻና የመዝጊያ ቡራኬ የሰጡት የኢህአዴግ ካድሬዎች የእምነት ተቋማት ምን ያህል ነጻነት የሌላቸው አጎብዳጅና ታዛዥ መሆናቸውን ያረጋገጠ ነው።

ያስቀየሙትን፣ የገደሉትን፣ በቂም የሚቀጠቅጡትን፣ የሚያስሩትን፣ የሚያሳድዱትን ህዝብ ይቅርታ በመጠየቅ ወደ እውነተኛ እርቅ መምጣት የተቀደሰ ሃሳብ ቢሆንም እነሱ ግን አርከሰውታል። ህዝብ በማንኛውም ጉዳይ እንዳያምናቸው ከማድረግ የዘለለ ውጤትም አያመጡም ሲሉ አስተያየት ሰጪዎችህ ተናገረዋል። ሃይለማርያምን አውቀዋለሁ የሚሉ አስተያየት ሰጪ እርሱን አባል አድርጋ የምትጓዝ የሃዋርያት ቤተክርስቲያን ዝምታን መምረጧ አሳዛኝ እንደሆነ አመልክተዋል።

ሃይለማርያም አሁን ድረስ በቤተክርስቲያኒቱ አባልነት ታቅፎ የተያዘ መሆኑንን የጠቆሙት አስተያየት ሰጪ፣ “ቤተክርስቲያን በገሃድ ህዝብ ላይ የጦርነት አዋጅ ያወጀን ሰው ተሸክማ ስትሄድ ዝምታ አግባብ አይደለምና ምዕመናን ይህንን ጥያቄ በማንሳት አስቸኳይ መልስ እንዲሰጣቸው ሊጠይቁ ይገባል። ይህ ካልሆነ የሃዋሪያት ቤተክርስቲያን በሃይለማርያም ታዛዥነት ለፈሰሰው የንጹሃን ደም እውቅና የመስጠት ያህል ይቆጠርባታል” ብለዋል። አያይዘውም የቤተክርስቲያኗ ዓለምአቀፍ አገልግሎት (ሚኒስትሪ) ይህንን እንዲያውቀው የሚመለከታቸው ሁሉ ደብዳቤ በመጻፍ እንዲያጋልጡ ጠይቀዋል። በተለይም የሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎች ለዚህ ጉዳይ ይፋዊ ምላሽ እስኪሰጥ ድረስ ገፍተው እንዲሄዱ አሳስበዋል። ቤተሰቦቻቸውም ቢሆኑ ከዚህ አይነቱ ጉዳይ ራሳቸውን ነጻ ማድረጋቸውን በይፋ ሊመሰከሩ እንደሚገባ ጠቁመዋል።

የዝግጀት ክፍላችን ይህንን ጉዳይ አስመልክቶ አስተያየት ለሚልኩ ሁሉ በሩ ክፍት ሲሆን ለተጠቀሰው የሃዋሪያት ቤተክርስቲያን ኦፊሳላዊ ጥያቄ እንደሚያቀርብ ከወዲሁ ለማሳወቅ ይወዳል። (ፎቶ: Getty Images እና ዋኢማ)

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ®