Wednesday, 31 December 2014 11:51

                ላለፉት 28 ዓመታት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በመምህርነት ያገለገሉት ዶ/ር መረራ ጉዲና ከኮንትራት ቅጥር አፈፃፀም ጋር በተያያዘ ከዩኒቨርሲቲው ጋር አለመስማማታቸው ታወቀ።

ዶ/ር መረራ ስለጉዳዩ ከሰንደቅ ጋዜጣ ተጠይቀው ካለፈው ሐምሌ ወር 2006 ዓ.ም ጀምሮ ጡረታ እንዲወጡ እንደተጠየቁና ጥያቄውን እንዳልተቀበሉት ተናግረዋል። ለዚህም የሰጡት ምክንያት አንድ ለጡረታ የደረሰ ሰው ሦስት ዓመት እንዲራዘምለት መጠየቅ የሚችልበት የሕግ አግባብ ስላለ ነው ብለዋል። ከሐምሌ 2006 ዓ.ም ጀምሮ የዩኒቨርሲቲው የሶሻል ሳይንስ ኮሌጅ በኮንትራት እንዲሰሩ የቀጠራቸው መሆኑን አስታውሰው ሆኖም የዩኒቨርሲቲ ፐርሶኔል ክፍል ቅጥሩን አልቀበልም በማለቱ እስካሁን ጉዳዩ በእንጥልጥል ላይ መሆኑን ገልፀዋል። በዩኒቨርሲቲው የሴኔት ሕግ መሠረት ኮሌጆቹ የሚፈልጉትን መምህር የመቅጠር መብት እንዳላቸው በማስታወስ የፐርሶኔል ክፍሉ በማያገባው ገብቶ ቅጥሩን ከልክሏል ብለዋል። ከዚሁ አለመግባባት ጋርም ተያይዞ ላለፉት ስድስት ወራት ደመወዛቸው መቋረጡን ጠቅሰው፤ ከዩኒቨርሲቲው ጋር ያላቸውን ሁኔታ ተከታትለው መፍትሄ ከጠፋ መብታቸውን በሕግ ለማስከበር ማሰባቸውን ጨምረው ገልፀዋል።

በጉዳዩ ላይ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን ለማነጋገር ያደረግነው ጥረት ለጊዜው አልተሳካም። ዶ/ር መረራ ጉዲና ከዩኒቨርሲቲው መባረራቸውን ሰሞኑን በአንዳንድ ማኅበራዊ ድረገጾች መዘገቡም አይዘነጋም።

 

Leave a Reply