እንደ ፈረንጆቹ አቆጣጠር ማርች 17, 2017 በኢትዮሚድያ ድህረ ገፅ ላይ በወጣ ፅሁፍ ላይ ወለላዬ ከስዊድን የተባሉት ፀሀፊ “እምዬ ምኒልክ ወላዋይ ነበሩ ወይ?” ሲሉ አበክረው ይጠይቃሉ።

መሃልም ወለላዬ ጋዜጠኞችና ተመራማሪዎች የትናቹ፤ ዝም አትበሉ ሲሉ ይማፀናሉ። የጥሪያቸው ምክንያትም የስዊድን ሶሻል ዴሞክራት ተቀጥላ የሆነው የኢትዮጵያ ሶሻል ዴሞክራት ማኅበር የአድዋን ድል በዓል ምክንያት በማድረግ ባዘጋጀው ዝግጅት ላይ የመጨረሻው ተናጋሪ ያደረጉት ንግግር ነበር። እኝህ ሶስተኛ ተናጋሪ ፕሮፌሰር ተከስተ ነጋሽ ይባላሉ። በድህረ ገፅ ላይ የሚገኝ መረጃ እንደሚያሳየው ፕሮፌሰር ተከስተ አስመራ ኤርትራ የተወለዱ ብዙውን ዘመናቸውን ደግሞ ስዊድን ውስጥ በታሪክ መምህርነትና ፀሀፊነት የሰሩ ሰው ናቸው። ብዙዎቹ የጥናት ፅሁፎቻቸውም በኤርትራ የቅኝ ግዛት ታሪክ ላይ ያተኮሩ ናቸው። አድዋን በተመለከተም እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በዐስራ ዘጠኝ ዘጠና ስምንት አ.ም. ካበረከቱት “አደዋና የኤርትራ ታሪክ የተወሰኑ የግዜ አቀማመጥ ጉዳዮች” ከሚል  የመፀሀፍ ምእራፍ በቀር የሰሩት ጥናት እንደሌለ የግል የህትመት መሃደራቸው ያሳያል። ይህ ፅሁፍ በተከስተ የሂወት ታሪክ ላይ፣ ብሔርና ማንነት ወይም ግለሰባዊ ባህሪያት ላይ ያተኮረ አደለም። ትኩረቱ በቅርቡ ስለአደዋና አፄ ምኒልክ ያደረጉት ትንታኔ ነው።

መቶ ሃያአንደኛው የዐደዋ የድል በዐል በዐለም ላይ በድምቀት ተከብሯል። ሲከበርም የማያጠራጥረው ታላቁ የአፍሪካውያን ድል መሆኑ ታምኖበት ነው። ዐደዋ አፍሪካን አሸናፊና የሚኮራባት እንጂ ተጎጂና ማፈሪያ አላደረጋትም። ዐደዋ እንዲያውም ብዙ ፈረንጆችና ኣፍሪካውያን እንደኛ ያሸነፉበትን ሳይሆን ከቅኝ መገዛት ነፃ የወጡባቸውን ቀናቶች ከሚያከብሩበት መጠን በታች ነው እያከበርን ያለነው። ከዚህም በላይ ሞቅ ደመቅ ማለት አለበት።

በወለላዬ ላይ ተጨማሪ ሃሳብ እንደ ወለላዬ ፅሁፍ ከሆነ ተከስተን በዝግጅቱ ላይ ግርምት ከፈጠሩባቸው ነገሮች አንዱ ከፕሮፌሰር ዮናስ ሬይሞንድና የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዝዳንት ሚስተር ታቦ ምቤኪ ስለአድዋ ከዳረጓቸው የቆዩ በቪዲዮ የተቀረፁ የቃለመጠይቅና የመድረክ ንግግር በሁዋላ እንዲናገሩ መደረጋቸው ነው። ይሔ ምኑ ያስገርማል? ግራስ ያጋባል? ይህን ነጥብ እንተውና ስለ ትልቁ ጉዳይ እንነጋገር።

ወለላዬን እርስ በርስ የሚጣረስ ምሁራዊ ያልሆነውን የተከስተን ንግግር እንዲህ ቀድቶታል “እኔ ያለኝ ወይም የማውቀው የአድዋ በዓል ታሪክ ከነሱ የተለየ ሲሆን፣ በተለይ ደግሞ ምቤኪ ከኔ ጓደኛ ከማሞ ሙጨ ደቡብ አፍሪካ ውስጥ ያጠናውን ይዞ ነው የቀረበው” ብለዋል። “ምቤኪ ከማሞ ሙጨ የተማረውን በትክክክል ይዞ  ማስተላለፍ ችሏል፤ ከኔ ቢማር ደግሞ የበለጠ እውነተኛ ታሪክ ማወቅ በቻለ ነበር”

እ ተ ጌ ጣይ ቱ እ ና አ ፄ ም ኒልክ
ይህችን ቅንጭብ ጥቅስ እስቲ በታትነን እንመልከታት። ተከስተ በመጀመሪያ “እኔ ያለኝ ወይም የማውቀው” በማለት ሃሳባቸውን ይከፍታሉ። እነዚህ ጥሩ የሆነ ምሁራዊ የመሐበረሰብ ሳይንስ አጥኚ የተለመደ አስተያየት ማቅረቢያ ቃላት ናቸው። ሁላችንም እኛ የምናቀውን እስከማውቀው ወይም እስከምረዳው ድረስ ብለን እንጀምራላን እንጂ ሀቁ ይሄና የኔ ብቻ ነው ብለን አንጀምርም። ነግር ግን ጥሩ የጀመሩትን ሃሳብ ፕሮፌሰር ተከስተ ወዲያው በመደምደሚያቸው ላይ “ከኔ ቢማር ደግሞ የበለጠ እውነተኛ ታሪክ ማወቅ በቻለ ነበር” ብለው ያበላሹታል። የሳቸውን የታሪክ አረዳድ “የበለጠ እውነተኛ ታሪክ“ የሚያደርገው ምንድን ነው? እንዴትሥ ደግሞ አንድ ፕሮፌሰር እኔ የተሻልኩ እውነት አዋቂ ነኝ ብሎ ይናገራል?

ሌላው ትልቁ የተከስተ ሃሳብ ውስጥ የሚታየው ያልተጣራ ድምዳሜና ጥፋት ሜቤኪን የማያነቡ የማይመራመሩ አድርገው ማቅረባቸው ነው። ምን ያህል አፍሪካውያን ስለኢትዮጲያ ታሪክ ከኛ በበለጠ እንደሚያነቡና እንደሚያቁ ዘንግተወት ነው ወይስ? ሚቤኪ ደሞ ከምሁር አፍሪካውያን መሪዎች አንዱ ነው። ከፕሮፌሰር ማሞስ ተምረውት ቢሆን ይህ የሚያኮራአደለም እንዴ? ፕሮፌሰር ማሞ ሙጬ ዘርፈ ብዙ የሆኑ የትምህርት የማስተማርና የምርምር ስራዎችን የሰሩ የሚያኮራ : ወግንንም የሚያስከብር በዙ ስራ የሰሩ ሊቅ ናቸው።

እንደ ወለላዬ ዘገባ  ፕሮፌሰር ተከስተ አደዋን በተመለከተ እሳቸው እንደሚገነዘቡትና ወደጣሊያን የተላለፉ መልክቶች አስተማማኝ መረጃ መሆናቸውን ገልፀው የሚከተሉትን ድምዳሜዎች አስቀምጠዋል።

የአፄ ምኒልክን የአመራር ደካማነት፣ የተላበሱትም ዝና ከሠሩት በላይ የተጋነነ ስለመሆኑ፤ ራስ መኮንንም ከአፄ ምኒልክ የተሻሉ እንዳልነበሩ፤ እቴጌ ጣይቱ አርቆ አስተዋይ እንደነበሩ፣ ነገሮችን የመፍታት ብቃታቸው ጠንካራ እንደነበር፤ በጦርነቱም ጊዜ የሳቸው (የቴጌ ጣይቱ) ብልህ አመራር ባይኖር የጦርነቱ ሁኔታ አሁን የያዘውን መልክ ይለወጥ እንደነበር፣ ይህንንም ሊረዱ የቻሉት ከኢትዮጵያ ወደጣሊያን በዚሁ ጉዳይ የተላለፉ መልክቶች በመኖራቸውና ያም አስተማማኝ መረጃ ስለመሆኑ፤ የአድዋ ድል በዕድል ወይም በአጋጣሚ የተገኘ ድል ስለሆነ፤ ይሄን ያህል መጋነን እንደማይገባው፤የተገኘው የድል ትርፍም እጅግ ጎልቶና ተጋኖ የተነገረለት እንደሆነ፤ በወቅቱ ከነበሩ ኢትዮጵያዊ የታሪክ ጸሐፊዎች ይልቅ እውነተኛውናትክክለኛው ታሪክ ሰፍሮ የሚገኘው በጣሊያን ታሪክ ጸሐፊዎች እንደሆነ፤ የነሱን ጽ ሁፍ ያላካተተ ታሪክ ዕውነተኛነቱ የሚያጠራጥር እንደሆነ፣ በአበሻው የሚነገረው ታሪክ በቃል ካንዱ ወዳንዱ የተላለፉ መረጃ የጎደላቸው ናቸው የሚሉ ነበሩ።

ከላይ ተቀንጭቦ ከተወሰደው የወለላዬ ዘገባ መመልከት እንደምንችለው፣ ሶስት ነገሮችን መረዳት ይቻላል። ምኒልክን የማኮሰስ፤ የኢትዮጲያ ፀሃፍትናን መረጃዎችን ከጣልያናውያን አሳንሶ ማየትና የዐደዋ ድልን ዝቅ አድርጎ ማቅረብ። ይህን መሰል ፅሁፎችና አስተሳሰቦች ሲቀርቡ የመጀመሪያቸው አደለም። ይህን ምን አልባት ለየት የሚያረገው በታሪክ ምሁር መቅረቡና አቀራረቡም ሳይንሳዊ አለመሆኑ ነው። መጀመሪያ አፄ ምኒልክን ደካማ መሪ ብሎ የሚደመድም የታሪክ ምሁር በተለይም አድዋን በተመለከታ: ተከስተ ከመጀመሪያዎቹ መሆን አለባቸው።

በሁለት ምክኒያት አንደኛ አደዋ የምኒልክን ደካማ አለመሆን ያስመሰከረ ድል መሆኑ : ሁለተኛው ደሞ “ደካማ” የሚል ድምዳሜ (claim) ማድረጋቸው ነው። አንድ የሶሻል ሳይንቲስት ማንኛውንም አይነት ክሌም በቀላሉ አያደርግም: ካደረገም በቅንፍ ያንን ትልቁን ቃል ያገኘበትን ቦታ ጠቅሶ ነው። ብዙ የታሪክ ፀሃፊዎች ታርክን እንደትረካ ይፅፉታል ከዛም የራሳቸውን ትንታኔ ፅፈው ይደመድማሉ። ከዐፈ ታሪክ ውጭ በፅሁፍ የተገኘ ታሪክ ቋንቋ ነው።ቋንቋ ደግሞ የቋንቋ ጥናት ስልቶችን የተከተለ ጥናት ያስፈልገዋል። እናም በጣም አግዝፈውና አክብረው ካመሰገኗቸው የጣልያን ፀሃፍት መሃከል ስንቱን የታሪክ የጥናት ስልት ብቻ ሳይሆን የቋንቋ የጥናት ስልትን ተጠቅመው አጠኑ? አንዱ የጥናት መንገድ ለምሳሌ ዲስኮርስ አናሊሲስ (Discourse Analysis)
ይባላል። ይህ ስልት ወቅቶችንና ፅሁፎችን በዘመኑ፤ በባህሉ፤ በፀሃፊው ግላሰብና ድርጅት፤ በስዋሰው፤ በዐይዲዎሎጂና በቅኔያዊ የቋንቋ አረዳድ፤ትንታኔና አፈታት በመታገዝ ታሪክን ይረዳል። ይህ በብዙ የታሪክ ነክ ፅሁፎቻችን ውስጥ ጎሎ ይታያል። ለምሳሌ አፄ ምኒልክን የጣሊያን ጋዜጦች እንዴት አድርገው ነበር በአደዋ ጦርነት ወቅት የገመገሟቸው የሚል የምርምር ጥያቄ ብናነሳ መጀመሪያ የዛን ግዜ ጋዜጦችን መሰብሰብ፤ ስለሳቸው የፃፉትን ሰብስቦ መረዳት ከዛም  የቋንቋና የጥናት መንገዶችን በመጠቀም መርምሮ ድምዳሜ ላይ መድረስ ይቻላል። በዛን ወቅት ከነበሩት የጣልያን መዛግብቶች ስለ ሚንልክም ሆነ ስለሃገራችን ሙገሳን መጠበቅ ሞኝነት ነው።

በግሌ ለምሳሌ ወደ መቶ የሚደርሱ ስለ አፄ ምኒልክ በዐደዋ ጦርነት ወቅት የታተሙ ጋዜጦችን አጥንቼ ነበር። አብዛኞቹ የጋዜጦቹ ፀሀፍት በሰሜኑ የኢትዮጲያ ክፍል ከጣልያን ወታደሮች ጋር የነበሩ ጣሊያንናውያን ናቸው። አልያም የአሜሪካን ጋዜጦች ዘገባዎቹን የወሰዱት ከጣሊያን ሚዲያዎች ላይ ነበር። የጥናት ውጤቱ እንደሚያሳየው ብዙዎቹ ዘገባዎችና ሀታተዎች ምኒልክንና ኢትዮጲያን በቅኝ ገዥ ልቦና፤ በዘረኝነትና በዝቅተኝነት የሚመለከቱና የተነተኑ ነበሩ። ይሄ ግን ሊግርም አይገባም። ምክኒያቱም ሊገዙ የመጡ ሃይሎች ናቸው። ብሎም የምእራባውያን ሚዲያ አፍሪካን ከዚህ በተለየ ተመልክቶና ዘግቦ እሚያቅ ከሆነ በጣም ጥቂት ነው። ይህን ይዞ የሚከራከር ምሁር ካለ ይሔ ችግር ነው። ምክኒያቱም እነዚህ ዘገባች ራሳቸው ውስብስብ የሆነ የቋንቋ ጥናት (Critical Discourse Analysis) ያስፈልጋቸዋል። ምኒልክ ድል ካደረጉ በዃላ ግን ጋዜጦቹ ወዲያው ስለምኒልክም ስለጥቁር ህዝብ ያላቸው የዘገባ ቃና ተለውጧል።  ነገር ግን እነዚህ ጋዜጦች ምኒልክን ለማኮሰስ ከተጠቀሙባቻው ቃላት መካከል በፍፁም የማይገኘው ደካማ  እሚለው ነው። እቴጌ ጣይቱንም በተመለከተ የወጡ ዘገባዎች በጥናቱ ውስጥ ተካተዋል። ብዙዎቹ ፅሁፎች የንግስቲቱን ውበትና ዝና ያሞካሹ ነበሩ። በአደዋ ድልም ላይ ስላላቸው ተሳትፎ አጉልተው ዘግበዋል። ተከስተም ብዙ አለተሳሳቱም። ነገር ግን ምኒልክን አኮሰስኩ ብለው ይልቁንም አገዘፏቸው እንጂ። የቱኛው ንጉስ ነው ሚስቱን የሚሳማ፤ የቱ ንጉስ ነው ሚስቱን ውጊያ እንድትመራ ያደረገ፤ የቱ ንጉስ ነው ለቤተሰቡም ለሃገሩም ለጠላቱም የሴትን እኩልነት በተግባር ያሳየ፤ ለዛውም በዚያ ዘመን? ባልና ሚስት ተደጋጋፊ ናቸው የምኒልክ ድል የጣይቱ እጅ አለበት የጣይቱም ልእልና ውስጥ የምኒልክ እጅ አለ። ባልና ሚስትን አሳንሶ በማቅረብ የሚነሳ ክርክርም ሆነ ፅሁፍ መንደራዊ ነው።

ሌለው “ጦርነቱን ኢትዮጵያ ያሸነፈችው በዕድል ነው። የተገኘውም ዕድል አንዱ የጣይቱ በዛን ዘመን ላይ መገኘት፤ ሁለተኛው ደግሞ የጣሊያን ሠራዊት ባወጣው እቅድ መሰረት አለመገናኘቱ ነው” የሚለው የፕሮፌሰር ተከስተ ድምዳሜ ግን ብዙም ጠለቅ ያለ ምላሽ የማያስፈልገው ማንኛውም ስለ ጦርነት ያነበበ የነገሮችን ወይም የሲስተምስ ኮምፕሌክሲቲን የሚረዳ ሰው ፈገግ ብሎ የሚያልፈው ነው።

ምኒልክ ታላቅ ባይሆኑማ የፈረንሳይ ሽቶዎች፤ የብራዚል ጋዜጦች፤ የአፍሪካ መንገዶችና ሌሎችም በሳቸው ባልተሰየሙ። በ1906 የወጣው ዋሽንግተን ታየምስ ምኒልክ ከሁሉም ነገስታት በላይ ዲሞክራቲኩ ባላሏቸው ነበር። የምኒልክን ደካማ አለመሆን እንዲሁም ወላዋይ አለመሆን ለማስረዳት ሌላ ዙር ጥልቀት ያለው ፅሁፍ መፃፍ ያስፈልጋል።

በመጨረሻም በአሁኑ ወቅት ታርክን በመረጃ አስደግፎ እውነትን ፍለጋ የሚደረግ ምሁራዊ የሃሳቦች ክርክር በጣም አሰልችና አድካሚ እየሆነ መጥቷል። ምክንያቱም ምሁሩም፤ ፖለቲከኛው፤ ታዛቢውም ታሪክን እየተነተኑ ያሉት ከእያንድአንዳቸው የብሄር፤ የሃይማኖትና የፖለቲካ መሰረት አንፃር በመሆኑ። ይሄ ደግሞ ክርክሩንና ውይይቱን አዙሪት፤ ተከራካሪውን ደግሞ “አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት …” ያደርገዋል።

ፀሃፊውን በዚህ አድራሻ ማግኘት ይቻላል: tedlad28@gmail.com (ይህ ጽሁፍ በቅድሚያ የወጣው ከ ደ ብርሃን ብሎግ መሆኑን ኢትዮሚድያ ይገልጻል)  March 24, 2017

Source       –      Ethiomedia