May 18, 2017
ዘመንም እንዲህ ያረጃል። ወርቃማውን የክርስትና ዘመን እንናፍቃለን!
መስቀሉ አየለ
ከአለም ዙሪያ ካሉና ጉዳዩ ስጋት ላይ ከጣላቸው በአስር ሽዎች የሚቆጠሩ ምእመምናን የአዲስ አበባውን ቅዱስ ሲኖዶስ በስልክ፣ ኢሜይልና በማህበራዊ ድህረገጾችን በመጠቀም ከዚህ አሳዛኝኝ ጥፋት እንዲታቀብ የተቻላቸውን ያህል ርብርብ ቢያደርጉም ሲኖዶሱ ጆሮ ዳባ ልበሱ ብሎ አንዱን በብልግናው የማይታማ፣ የስብሃት ነጋ የመንፈስ ልጅ የሚሆን ነውረኛ ኢ–ኦርቶዶክሳዊ ፓስተር እና አንድ ልማታዊ “መነኩሴ” ደግሞ በቀጥታ ከጋምቤላው አስተዳዳሪ በተጻፈ የትዕዛዝ ደብዳቤ “ለጵጵስና” ሹመት አቅርቧቸዋል።
ከስልሳ ሚሊዮን ያላነሰ ምዕመምን ያላት ቤተክርስቲያን ታዛቢ እንደሌለው ቤት ማንም ከምንም ተነስቶ ወደ ላይኛው መንበር የሚሰቀልባት ሆናለች። ይኽ ሁሉ ሲሆን ደግሞ ለተወሰኑ ቀናት ከንፈር ከመምጠጥ ውጭ የተጨበጠ ተቃውሞ የሚያደርግ ወይንም ለቤቱ የሚቀና ቆፍጣና ወጣት የለም።
“የቤትህ ቅናት በላኝ” ተብሎ በወንጌል የተጻፈውንና ባለቤቱ ስለ መቅደሱ ባለው ክብር ሸቃጩን ሁሉ በጅራፍ እየገረፈ ስለማውጣቱ የተነገርው ያለም አይመስልም። ወያኔ እንደ እነዳንኤል ክብረትን በመሰሉ ከገዥው መደብ ጎሳ ጋር የጋብቻ ዝምድና በፈጠሩ ልማታዊ ሰባኪያን በተቀመረ ዘዴ “ይዘን መጣን” ባሉት አዲሱ የስብከት መንገድ አንድ ሙሉ ፓሲቭ (ምውት) ጅነሬሽን የመፍጠሩ ሂደት እንደተሳካላቸው በፍሬው ይታወቃል። በአንድ ወቅት ከወያኔ ተሰርቆ በወጣው ዳጎስ ያለ ጥናት ላይ ሰፍሮ እንደተገኘው “ወጣቱን ከነቴዲ አፍሮ አይነት አስተሳሰብ በማውጣት በተጠና መንገድ ወደ እነ ዳንኤል ክብረትን መንገድ መግፋት..” የሚል እንደነበር በኢሳት ቴለቪዥን ተለቆ ያየነውን ሃቅ ልብ ይሉዋል።
–አገሬ በሰማይ ነው የሚል፤
–ሁሉም ነገር በሃጢያቴ ብዛት የመጣብኝ ችግር ነው የሚል፤
–እግዚአብሔር ያውቃል በሚል ሽፋን ተጀቡኖ ለራሱ ሃላፊንትን የማይቀበል፤
–በአገሩ ጉዳይ ያገባኛል ማለትን እንደ ሃጢያት የሚያይ፤
–ምንም ይሁን ምን ንጉስ የሚነግሰው በእግዘ አብሔር ፈቃድ በመሆኑ እርሱን ማውረድም ሆነ ማስቀጠል የ እግዚ አብሔር ድርሻ በመሆኑ የኔ ድርሻ ነገስታቶችን ልብ እንዲሰጣቸው መጸለይ ብቻ ነው ብሎ ከልቡ የሚያምን፣ –ነጠላ ለብሶ ጧፍ ስላበራና ከበሮ ስለመታ ብቻ የሚጠበቅበትን ሃላፊነት የተወጣ የሚመስለው; የተሰለበ ትውልድ የመፍጠሩ ሂደት በተወሰነ ደረጃ አልተሳካም ማለት አይቻልም።