May 26, 2017
ወደፊት አዲስ አበባ እንዴት እንደምትሆን መገመት ከባድ ቢሆንም የአዲስ አበባ ጉዳይ ያገባናል ብለን ለምናም ሰዎች፤ ሳያገባቸው ገብተው አያገባችሁም የሚሉንን ንቀን በመተው፤ አንድ አንድ ጉዳዮች ላይ ማተኮር ያለብን ይመስለኛል፡፡ እነዚህ የወደፊት አገር ተረካቢ የምንላቸው ህፃናት እና ወጣቶች ጉዳይ ሊያሳስበን ይገባል፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ በተለይ በየቀኑ በምመላለስበት ለገሐር፣ ብሔራዊ ቲያትር/መከላከያ መብራት ላይ፣ መስቀል አደባባይ፣ ወዘተ የምናያቸው ህፃናት ልጆች በዚህ ሁኔታ መኖራቸው እንዲያበቃና አስቸኳይ መፍትሔ እንዲያገኝ አንድ ቀን ተነስተው በከተማው ያለውን ህንፃና መኪና በድንጋይ ሲያወድሙ፣ እሳት ጭረው ሲለኩሱ መሆን ያለበት አይመስለኝም፡፡ በተጨማሪ ከተማው የተስፋፋው ህፃናትን አዝሎ ልመና በከፍተኛ ሁኔታ የሚስተናገደው፤ የሴቶችና ህፃናት ሚኒሰትር ቢሮ ባለበት ጎዳና ላይ ነው፡፡ በሰማቸው ሚኒሰትርም ይሁን ኤክስፐርት የሆኑ ሰዎች ይህ ጉዳይ እንደሌለ ቆጥረው በተንደላቀቀ መኪና ሲገቡና ሲወጡ ስራቸው ምን እንደሆነ ሊገባኝ አይችልም፡፡
በአንድ ወቅት የቀደሞዋ የሴቶችና ሕፃናት ሚኒሰትር በጉዲፈቻ ወደ ውጭ ስለሄዱት ህፃናት ጉዳይ ለመነጋገር ፈረንሳይ መሄዳቸውን አስታውሳለሁ፡፡ አፍንጫቸው ስር ቤንዚልና ማስተሸ እየሳቡ በጠራራ ፀሀይ ናላቸውን እያዞሩ የሚገኙትን ህፃናት ለመታደግ ግን አንድም የሚደረግ ነገር አይታይም፡፡ በዚህ ፅሁፌ ወቀሳ ብቻ ሳይሆን የመፍትሄ አቅጣጫም ማስቀመጥ እፈልጋለሁ፡፡
-
በመንገድ ላይ የሚገኙ እድሚያቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ በተለይ በቤንዚልና ማስትሽ ናላቸውን የሚያዞሩት ህፃናት እንደዚህ መሆን መብታቸው ሰለአልሆነ፣ በግዳጅ ወደ አንድ ማዕከል ገብተው ተገቢውን ድጋፍና እንክብካቢ እንዲያገኙ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ እነዚህ ህፃናት በማሳደጊያ ወይም በጉዲፈቻ እንዲኖሩ ማመቻቸት በወረቀትም ቢሆን ሕገ መንግሥታዊ ድንጋጌ አለ (አንቀፅ 36)፤ እነዚህ ሕፃናት ምግብ፣ መጠለያ፣ ትምህርት የማግኘትና ጤናቸው የመጠበቅ መብት አላቸው፡፡ መንግሰት ይህን የማድረግ ግዴታ አለበት፡፡
2. ሕፃናትን ለልመና መጠቀም ወንጀል ነው፡፡ ማንኛውም ሰው ወላጅ እናትም ሆነ አባት ቢሆኑ ህፃናትን ለልመና ሲጠቀሙ ዝም ብሎ መመልከት፤ ይልቁንም ለእነዚህ ሰዎች ገንዘብ በመስጠት ማበረታታት ገደብ ሊደረግበት ይገባል፡፡ ልጆቻቸውን መመገብ አልቻልንም ብለው በልመና ላይ የተሰማሩ ሰዎች፤ ልጆቻቸውን ተቀምተው ልጆቹ አስፈላጊው ድጋፍና እንክብካቤ እንዲያገኙ ማድረግ የመንግሰት ግዴታው ይመስለኛል፡፡
የአረጋዊያን መጦሪያ እንደሚያስፈልግ ሁሉ የህፃናት ማሰደጊያ ቦታ መኖር የግድ ነው፡፡ የህፃናት ማሳደጊያ የመጨሻው አማራጭ እንደሆነ እረዳለሁ፡፡ ነገር ግን ሕፃናት በጎዳና ላይ በዚህ ሁኔታ ከሚኖሩ ግን መቶ በመቶ የተሻለው አማራጭ የህፃናት ማሰደጊያ ስፍራ ነው፡፡ ይህን ለማድረግ ይህች አገር አቅም የላትም የሚባል ሰንካላ ሰበብ መቅረብ የለበትም፣ ስርዓት ተዘርግቶ ሁላችንም የበኩላችንን ማድረግ እንፈልጋለን፡፡ እነዚህ ህፃናት ማቆያዎች በጉዲፈቻ ልጆች ማሳደግ ለሚፈልጉም ግለሰቦችም ሰርዓት ዘርግቶ ሊያስተናግድ ይችላል፡፡