May 28, 2017 08:34

 

የግሪክ፣ የካቶሊክ፣ የሶርያ፣ የሕንድ፣ የሩሲያ፣ የግብጽ እና የኢትዮጵያ አብያተ ክርስቲያናትን ስንክሳሮች ለማየት ሞክሬያለሁ፡፡ በእነዚህ ቀደምት አብያተ ክርስቲያናት ለቅድስና የበቁ አባቶች እና እናቶች ታሪክ ጾም፣ ጸሎት፣ ትምህርት፣ ሱባኤ፣ ትኅርምት፣ ተጋድሎ፣ ሰማዕትነት፣ በድፍረት መመስከር፣ ንጽሕና፣ ተባሕትዎ፣ ለሰዎች በጎ ነገር ማድረግ፣ ለሌሎች መሠዋት አና ሌሎችንም የእምነት እሴቶችን እናያለን፡፡ ማጭበርበርን፣ ማታለልን፣ ስለላን፣ ዘረፋን እና ጥፋትን በቅድስና መንገዳቸው ውስጥ ፈጽሞ አናገኘውም፡፡


የሂንዱይዝምን፣ የኮንፊሺየዝምን፣ የዞራስተሪዝምን እና የሌሎችንም የቀደምት ሰዎች እምነቶችንም እንይ፡፡ ጾም እና ጸሎት፣ ምናኔ እና ተጋድሎ፣ ራስን መግዛት እና ይህንን ዓለም መናቅ፣ ማስተማር እና መማር፣ ለሰዎች በጎ ነገር ማድርግ እና ለሌሎች መሥዋዕት መሆን የእምነቶቹ መሠረታውያን እሴቶች ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡ ማጭበርበርን፣ ማታለልን፣ ስለላን፣ ዘረፋን እና ጥፋትን በቅድስና መንገዳቸው ውስጥ ፈጽሞ አናገኘውም፡፡
እነዚህ ነገሮች አንድ ነገር ያመለክቱናል፡፡ ሃይማኖት ስሙ እና ሕግጋቱ ቢለያዩም ከመማር እና ከማስተማር፣ ለራስ የእምነቱን ሕግጋት ከመጠበቅ፣ ከውሳጣዊ ንጽሕና እና ለሌሎች በጎ ነገር ከማድረግ ጋር ፍጹም የተገናኘ መሆኑን፡፡
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ተሳስታለች፤ መሥመርዋን ለቅቃለች ልናስተካክላት ይገባል ብለው የሚያምኑ ሰዎች መነሣታቸውን ከልዩ ልዩ ምንጮች ስንሰማ ከረምን፡፡ እኔ በሃሳባቸው መቶ በመቶ ባልስማማም፤ አንድ ሰው እንዲህ ብሎ ማሰቡ ግን መብቱ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡
የሚከራከርበትን ሃሳብ በግልጽ አውጥቶ፤ የማምነው እንደዚህ ነው ብሎ፣ የማይቀበለውን ኮንኖ በሠለጠነ መንገድ ሃሳቡን ካቀረበ ይኼ ሰው ጤነኛ ሰው ነው ብዬ አምናለሁ፡፡
እንዲህ ካለው ጤነኛ ሰው ጋር መከራከር፣ ሃሳቡን በሃሳብ፣ መጣፉን በመጣፍ፣ አባባሉን በአባባል፣ ነቀሳውን በነቀሳ መሟገት እና ቢቻል መግባባት ባይቻል ደግሞ ከነ ልዩነት መኖር ይቻላል፡፡
በቅርብ አመታት የምንሰማው ግን ከዚህ የከፋውን ነው፡፡ ይህንን ዓይነት አመለካከት የያዙ ሰዎች በመማር እና በማስተማር፣ በመከራከር እና በማስረዳት፣ በግልጽ አውጥተው በማሳየት እና በማሳመን ሳይሆን በማጭበርበር እና በስለላ፣ በማጥፋት እና በማውደም መንገድ እምነታቸውን ለማሥረጽ መሞከራቸውን አየን፡፡
ይኼ ከጤነኛነት ያለፈ መንገድ ስለሆነ እንቃወመው ዘንድ ግድ ነው፡፡
አንድ ሰው በታቦት ክብር እና ሃይማኖታዊ ዋጋ አላምንም ብሎ የሚያምነውን ማስተማር ይችላል፡፡ ከፈቀድን እንቀበለዋለን፤ ካልፈቀድን በጨዋ ደንብ አንቀበልህም እንለዋለን፡፡ እርሱ በታቦት ሥርዓት ስላላመነ የኢትዮጰያ ቤተ ክርስቲያን ታቦታትን ለማጥፋት፣ ለማስሰረቅ፣ አስሰርቆም ለመሸጥ ከተነሣ ግን ስለ እምነትም ስለ ሀገርም፣ ስለ መብትም ብለን ሰው የተባልን ሁሉ እንቃወመዋለን፡፡
አንድ ሰው በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አዋልድ መጻሕፍት ላይ ጥያቄ በመጠየቁ ጠላት ነው ብለን አናምንም፡፡ ምናልባት የተለየ አመለካከት ያለው ሰው እንለዋለን እንጂ፡፡ ከራሱ እይታ እና መረጃ ተነሥቶ «ስሕተት ናቸው» ብሎ ማስተማሩንም ባንወድድለትም እናከብርለታለን፡፡ ምናልባት ማስረጃውን በማስረጃ፣ ሃሳቡን በሃሳብ እየተነተንን መልስ እንሰጠው ይሆናል፡፡ ጠላታችን ነው ብለን ግን አንነሣበትም፡፡
ከዚህ ድንበር ተሻግሮ እርሱ የማይፈልጋቸውን አዋልድ መጻሕፍት ለማቃጠል፣ ለመቆንጸል፣ ከየዕቃ ቤቱ ወጥተው ወደ ባዕድ እጅ እንዲገቡ ለማድረግ፣ ብራናውን ለማበላሸት፣ ቀለሙን ለማጥፋት፣ ዕቃ ቤታቸውን ለማቃጠል ከተነሣ ግን ይህ በእምነት ብቻ ሳይሆን በሀገርም ላይ የተነሣ የታሪክ እና የቅርስ፣ የመብት እና የጤነኛ አስተሳሰብ ጠላት ነውና እንቃወመዋለን፤ እንታገለዋለንም፡፡
ገዳማዊ ሕይወትን የተቃወሙትን ሁሉ አንጠላቸውም፤ ስላልገባቸው ነው፤ የዕውቀት ማነስ ነው ብለን እንገምታለን፤ ያለበለዚያም ደግሞ ጫፋችንን እስካልነኩን ድረስ በዚህ መንገድ ማመን መብታቸው ነው ብለን እንተዋቸዋለን፡፡ ከዚህ አልፈው ወደ ገዳማት እየገቡ ቅርስ የሚዘርፉ፣ ሴት ገዳማውያንን የሚደፍሩ፣ የተሣሣተ መረጃ በገዳማት ውስጥ የሚነዙ ከሆነ ግን እምነታችንን ብቻ ሳይሆን ሰብአዊ እና ሕጋዊ መብታችንን ተዳፍረዋልና እናጋልጣቸዋለን፤ በሕግ መንሽም ለፍርድ ነፋስ አሳልፈን እንሰጣቸዋለን፡፡
አንድ ክርስቲያን እስልምና የተሳሳተ እምነት ነው ብሎ ሊያምን ይችላል፡፡ ይህንን አመለካከቱንም ማስተማር እና የተቀበሉትን ማሳመን ይችላል፡፡ የራሱ እምነት ከእስልምና የተሻለ ነው የሚልበትን ምክንያት እና ማስረጃ እያቀረበ መከራከር እና መሟገት መብቱ ነው፡፡
ከዚህ አልፎ መስጊድ ውስጥ ገብቶ የጸሎት ሥርዓትን መበጥበጥ፣ የመድረሳ ት/ቤቶችን ማፍረስ፣ የሙስሊም ልብስ ለብሶ ተመሳስሎ በመግባት የእስልምና እምነት አማኞችን ሰላም መንሣት፣ ቁርዓን ማቃጠል፣ የእስልምናን ጥንታውያን ቅርሶች ማጥፋት፣ በእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት የአሠራር ሥርዓት ውስጥ ሠርጎ የአሠራር ሥርዓቱን መበጥበጥ ከጀመረ ግን ከጤነኛ እና ከሕጋዊ መንገድ አልፏልና ከሙስሊሞቹ ጋር አንድ ሆነን እንቃወመዋለን፤ እንታገለዋለንም፡፡
ማንኛውም እምነት ሰይጣናዊነትን ይቃወማል፡፡ በራሱ በሰይጣን የሚያምን ካልሆነ በቀር፡፡ የሰይጣናዊነት ሁለቱ ዋና ዋና መገለጫዎች ደግሞ ክፋት እና ተንኮል ናቸው፡፡ በእምነት ስም ወንጀል ለመሥራት ካልታሰበ በቀር ከእምነት ጋር ክፋትን እና ተንኮልን አሥተሣሥሮ መጓዝ ወተት እና ኮምጣጤን አብሮ ከማኖር በላይ የማይቻል ነው፡፡
አሁን አሁን የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን እናድሳለን ብለው በተነሡ አካላት ዘንድ የምናየው እና የምንሰማው ነገር የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ በመቃወም የተነሣ ሌላ ንቅናቄ አይደለም፡፡ክፋትን እና ተንኮልን አንግቦ የተነሣ አለም አቀፍ ምስጥራዊ ማህበረስብ ሰይጣናዊ ንቅናቄ እንጂ፡፡ ዓላማውም ማደስ አይደለም፡፡ኦርቶዶክስን ማፍረስ እንጂ፡፡
እስካሁን ድረስ በየትኛውም የእምነት ታሪክ ውስጥ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ስለላን፣ ሤራን፣ ማፍረስን፣ ስርቆትን፣ ዘረፋን እና ማታለልን የእምነቱ ማራመጃ መንገዶች ያደረገ ብቸኛ የእምነት ንቅናቄ አለ ከተባለ እርሱ ዛሬ ዛሬ የምንሰማው «የተሐድሶዎች ንቅናቄ» ብቻ ነው፡፡
ትክክለኛ ነገር አለኝ፤ በያዝኩት ነገር አምንበታለሁ፤ ለያዝኩት ነገርም እከራከርበታለሁ፤ ማስረጃ እና መረጃም አለኝ፤ የኔ መንገድም የተሻለ ነው ብዬ አምናለሁ የሚል አካል ራሱን በይፋ ገልጦ፣ ፊት ለፊት ወጥቶ፣ ሃሳቡን አንጥፎ፣ ማስረጃውን አሰልፎ በብርሃን ይጓዛል እንጂ በጠላት ከተማ እንደ ገባ ሰላይ የድብቅ መንገድ አይጓዝም፡፡
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሕጋዊም መንፈሳዊም ተቋም ናት፡፡ መብቶቿ እና ጥቅሞቿ በሕግ ልዕልና ያላቸው ናቸው፡፡ ተቋሞቿ፣ ንብረቶቿ፣ ት/ቤቶቿ እና ቅርሶቿን የመጠቀም፣ የመጠበቅ፣ የመከባከብ እና ለትውልድ የማስተላለፍ መብት አላት፡፡ በእነዚህ ክልሎች ገብቶ ማንም ሌላ ወገን ያልፈቀደችውን ተግባር በድብቅ እንዳይፈጽም ሕግም ሞራልም ይከለክለዋል፡፡
አሁን እያየነው ያለነው ተግባር ግን የሃይማኖት አስተምሮን ተቃውሞ ሌላ የተሻለ አስተምህሮ የማምጣት ተግባር ሳይሆን ክፋት እና ተንኮልን ገንዘብ ያደረገ የሤራ ተግባር ነው፡፡ በገዳማት ገብቶ ብራና መፋቅ፣ የአብነት ት/ቤቶችን መበተን፣ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ውስጥ ገብቶ በርዳታ ስም ሀብቷን መበከል፤ ቅርሶቿን መዝረፍ እና መሸጥ፣ ጥንታውያን ተቋማቷን ማውደም፤ ታሪካዊ እና ጥንታዊ ንዋያተ ቅድሳትን እና መጻሕፍትን ማበላሸት በምን መመዘኛ ነው የሃይማኖት ሥራ የሚሆነው?
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የጥንታዊ የክርስትና ትምህርት ጠባቂ፣ የጥንታዊ እና ታሪካዊ የክርስትና ሀብቶች ባለቤት፣ የጥንታዊ መጻሕፍት ግምጃ ቤት፣ የቀደምት ኢትዮጰያዊ ባህሎች እና ትምህርቶች መገኛ፣ የሀገራዊ የአስተምህሮ ጥበብ ማዕከል፣ የቀዳሚ ክርስቲያናዊ ዜማ መፍለቂያ፣ በብዙዎች ዘንድ የጠፉ የአበው ድርሳናት ማከማቻ፣ ልዩ ክርስቲያናዊ ማዕከል ናት፡፡
በዚህች ቤተ ክርስቲያን ላይ በተንኮል እና በሤራ የሚደረግ ወንጀል ሁሉ በሦስት ነገሮች ላይ የሚሠራ ወንጀል ነው፡፡ በክርስትና ላይ፣ በሰው ልጅ ታሪክ ላይ እና በሀገር ላይ፡፡
በአንዳንድ የአውሮፓ ሀገሮች ተጀምሮ ምዕራቡን ዓለም መንፈሳዊነት ወደ ተለየው ክርስትና የከተተው የተሐድሶ ነፋስ በክርስትና እና በክርስቲያናዊ ሀብቶች ላይ የማይተካ ጥፋት አድርሷል፡፡ በወቅቱ በተቀሰቀሰው ስሜታዊነት በተሞላው ነውጥ ምክንያት አያሌ ክርስቲያናዊ ትምህርቶች እና ቅርሶች ላይመለሱ ጠፍተዋል፡፡ ከሁለት መቶ ዓመታት በኋላ ብዙ ሀገሮች ከቀበሩበት ሊያወጧቸው እንደ ዔሳው በዕንባ ቢፈልጓቸው ሊያገኟቸው አልቻሉም፡፡
በዚህ የተነሣ ታላላቅ የቅርስ ጥናት እና ጥበቃ ማኅበራትን አቋቁመው በሌሎች ሀገሮች ያሉ ቅርሶች ተመሳሳይ ውድመት እንዳይደርስባቸው የቻሉትን ሁሉ በፀፀት ሠርተዋል፡፡ በዚህ ዘመን ከደረሰው ጥፋት በእግዚአብሔር ቸርነት ከተጠበቁት ሀገሮች አንዷ ኢትዮጵያ ናት፡፡ ለዚህ ነበር አያሌ ሚሲዮናውያን እና አሳሾች ቅርሶቻችንን ሲዘርፉ እና ሲተረጉሙ የኖሩት፡፡
አውሮፓውያን በክርስትና ላይ የሠሩት የማይካስ ወንጀል አምላክ የለሽ ትውልድ እንጂ ጻድቃንን አላፈራላቸውም፡፡ ይህንን ወንጀል ኢትዮጵያ ላይ ለመድገም መነሣት ክርስትናን ያለ ጥግ ማስቀረት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ኦርጅናሌው ክርስትና ምን እንደሚመስል በትክክል ማሳየት ከሚችሉ ጥቂት ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናት መካከል አንዷ ናት፡፡ ለዚህ ነው በዚህች ቤተ ክርስቲያን ላይ በተንኮል እና በክፋት የሚደረግ ወንጀል ሁሉ በክርስትና ላይ የሚቃጣ ወንጀል (crime against Christianity) ነው የምንለው፡፡
በሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ ታላላቅ ለውጦች ካመጡት ታሪኮች ዋነኛው ክርስትና ያመጣው ለውጥ ነው፡፡ ለዚህም ነው የክርስትና ታሪክ ከሰው ልጆች ታሪኮች መካከል ዋነኛው ታሪክ የሚሆነው፡፡ ክርስትና ትምህርት ብቻ ሳይሆን አስተሳሰብ፣ የትምህርት መንገድ፣ ርዕዮተ ዓለም፣ የሥነ መንግሥት ምንጭ፣ ፍልስፍና፣ የሥልጣኔ መዘውር፣ የዓለምን መልክዐ ምድር ቀያሪ፣ የሥነ ጽሑፍ መንገድ፣ የሥነ ሥዕል መርሕ፣ የሥነ ጥበብ ትልም፣ የሥነ ዜማ ስልት፣ የሕዝቦች መገናኛ ድልድይም ሆኗል፡፡ በመሆኑም የክርስትና ሀብቶች እና ቅርሶች የአንድ እምነት ሀብቶች እና ቅርሶች ብቻ ሳይሆኑ የሰው ልጆች ሀብቶች እና ቅርሶች ሆነዋል፡፡ በእነዚህ ሀብቶች እና ቅርሶች ላይ እናድሳለን በሚሉ አካላት የሚሠነዘረው ጥፋት በሰው ዘር ሀብት ላይ የሚሠነዘር ጥፋት (crime against human heritage) የሚሆነውም በዚህ የተነሣ ነው፡፡
ጥፋቱ ከዚህም አልፎ ሀገራዊ መልክም አለው፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የኢትዮጵያን አብዛኛውን ሕዝብ የምትወክል፣ አስተሳሰቡን እና ርዕዮቱን የምትቀርጽ ተቋም ናት፡፡ ታሪኳ የሀገሪቱ ታሪክ፣ ባህልዋ የሀገሪቱ ባህል፣ ቅርሷ፣ የሀገሪቱ ቅርስ፣ ጥበቧ የሀገሪቱ ጥበብ፣ ዘመን መቁጠርያዋ የሀገሪቱ ዘመን መቁጠርያ ሆነዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ የሀሪቱ አንዷ እና ዋነኛዋ መገለጫ ናት፡፡ እናም በዚህች ቤተ ክርስቲያን ሀብቶች ላይ የሚሠነዘር ጥፋት ሁሉ በሀገር ላይ የሚቃጣ ወንጀል (crime against the mother land) ነው፡፡ የሚመለከተውም የቤተ ክርስቲያኒቱን አማንያን ብቻ ሳይሆን መላውን ኢትዮጵያዊ፣ የሀገሪቱን መንግሥት እና የኢትዮጵያን ወዳጆች ሁሉ ነው::
ኢየሱስና ሐዋሪያት በግልጽ እንጂ እንደ ማፊያ እና ሰይጣን በስውር በጓሮ በር አልገቡም ፤ክርስትና ስለላ፣ ሤራ፣ ዝርፊያ፣ውድመት እና ደባ አይደለም። የክርስትናም መንገድ ቀና እና ግልጥ እንጂ ተንኮል እና ክፋት አይደለም።ይህ የክርስትና ሃይማኖትን፤ሊያፈርስ፣ክርስትያኖች ፤ሊያርድ፣ ሊዘርፍ፣በተሃድሶ ስም የተደራጀ አለም አቀፍ የኢሊሙናንት ምስጥራዊ ቡድንን ኢትዮጲያዊ ሁሉ አንድ ሆነን ልንቃወመውና፤ ልናስቆመውምና በትልቅ ቁጣ ልንጋደለው ይገባል፡፡
Source    –  Daniel Kibret Blog