05 Jul, 2017 By 

ታደሰ ገብረማርያም 

የጨቅላ ሕፃናት የመንጋጋ ቆልፍ በሽታ ከኢትዮጵያ መወገዱን የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ ከሚኒስቴሩ የእናቶችና ሕፃናት ዳይሬክቶሬት የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ በሽታው ሊወገድ የቻለው ለነፍሰ ጡር እናቶች ክትባት በመስጠት፣ የማዋለድ አገልግሎቱን በሠለጠነ ባለሙያና ንጽሕናቸው በተጠበቁ የሕክምና መሣሪያዎች በማከናወንና የበሽታ ቅኝት በማካሄድ ነው፡፡

በሽታው መወገዱ የተረጋገጠው የተባበሩት መንግሥታት የሕፃናት አድን ድርጅትና የዓለም ጤና ድርጅት ባካሄዱት ጥናት ሲሆን፣ በከፍተኛ መጠን በተጠቁ 59 ዞኖች ላይ ከ1991 እስከ 2001 .. ድረስ በተካሄደው እንቅስቃሴ፣ 15 ሚሊዮን ነፍሰጡር እናቶች ክትባት አግኝተዋል፡፡

የበሽታው መንስዔ ከአፈርና ከቆሻሻ እንዲሁም ንጽሕና የጎደለው የወሊድ አገልግሎት መሆኑን፣ በዚህም የተነሳ በሽታው ሊጠፋ እንደማይችል ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል፡፡ መፍትሔውም በሽታው የተወገደበትን አካሄድ ቀጣይ ማድረግ መሆኑን አክለዋል፡፡

የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ዴኤታ ከበደ ወርቁ (/) የእናቶችና ሕፃናት ጤና ቅድሚያ ከሚሰጣቸው ሌሎች የማኅበረሰብ ጤና አገልግሎቶች ጋር በማስተሳሰር የተገኘው ውጤት ቀጣይነት እንዲኖረው በትኩረት እንደሚሠራ ተናግረዋል፡፡

የመንጋጋ ቆልፍ በሽታ ሁለት ዓይነት ሲሆን፣ የመጀመሪያው ከአንድ ወር በታች ያሉ ሕፃናትን ያጠቃል፡፡ ሁለተኛው ደግሞ በወሊድ ወቅት በማሕፀን ላይ በሚኖር ቁስል የሚፈጠሩ ባክቴሪያዎች የሚያመጡት ነው፡፡ 

ማህበራዊ

Author

anon