July 6, 2017 07:36

ሳሚ የሚባሉ ህዝቦች በሰሜናዊ ስካንዲኔቪያ እና ሩሲያ ይኖራሉ፡፡ ሬይንዲር ወይም የበረዶአማ አጋዘን የተባለውን እንስሳ በአንድ ሽህ የተለያዩ ስያሜዎች ይገልጹታል፡፡ ኢስኪሞ የሚባሉት በሰሜናዊ አሜሪካና ካናዳ የሚኖሩ ህዝቦች ለበረዶ ከ50 እስከ መቶ የሚሆኑ ስሞች ይሰጡታል፡፡ ማለትም በረዶን በ50 እና ከዛ በላይ የተለያዩ ስሞች በመጠቀም ይገልጹታል፡፡ በአረብኛ ቋንቋ ግመል አንድ ሽህ ስሞች አሉት፡፡ በአፋር ግመል ወደ 13 ስሞች አሉት፡፡ እነዚህ ህዝቦች ለተዘረዘሩት ነገሮች ብዙ ስም የሰጡበት ምክንያት ህይወታቸው በቀጥታ በእነሱ ላይ የተመሰረተ ስለሆነ ነው፡፡ ለሳሚዎች የበረዶ አጋዘን ማለት ጠቅላላ ህይወታቸው የተመሰረተበት ነው፡፡ ስለዚህም ከእሱ ውጭ ህይወት የማይታሰብ ነው፡፡ ለዛም በተለያዩ ስሞች ይጠሩታል፡፡ ለኢስኪሞ ወይም ኢኑይቶች ህይወት ያለበረዶ ምንም ነው፡፡ በረዶ ቤታቸው፤ መጠጣቸው፤ የአደን ቦታቸው፤ መዋኛቸው..ወዘተ ነው፡፡ ግግር በረዶ የለም ማለት እነሱ የሉም ማለት ነው፡፡ አረብና ግመል በቀጥታ የተያያዙ ስለሆነ አንድ ሽህ ስሞች የተሰየመበት ምክንያት የግመልን አስፈላጊነት የሚያመለክት ነው፡፡ ለአረብ ግመል ህይወት ነው፡፡ ለአፋርም እንደዚሁ፡፡ ግመል በአፋር ህይወት ውስጥ እጅግ መሰረታዊ ከመሆኑ የተነሳ በ13 የተለያዩ ስያሜዎች ይጠሯቸዋል፡፡ ስለዚህ ያለግመል ህይወት ለአፋር አስቸጋሪ ነች፡፡

የአማራን የህይወት ትስስር ስናይ መሬትን በቅድሚያ እናገኛለን፡፡ አማራ ያለመሬት ምንም ነው፡፡ መሬት በጣም ትልቁ ዋጋ ያለው ነገር ነው፡፡ ማንም አማራ ለመሬት የሚሰጠውን ዋጋ ለምንም አይሰጥም፡፡ በዚህም ምክንያት አማራ መሬትን በብዙ ስሞች ይጠራዋል፡፡ አማራ መሬትን መሬት፤ ምድር፤ ባድማ፤ ኩራ፤ ወጀድ፤ ጓሮ፤ ማሳ፤ ጥማድ፤ እርሻ፤ መስክ ወይም ሜዳ፤ ርስት፤ ጉልት፤ አገር፤ ሀገር፤ ውርስ፤ ድንጅ፤ ቀየ፤ መንደር፤ ዙሪያገባ፤ እትብት የተቀበረበት፤ ጉልማ፤ ድንበር ፈሰስ፤ ዞታ ወይም ይዞታ፤ ዲበ ቀብር፤ አጥቢያ፤ ግድም፤ ምሪት፤ እና ወዘተርፈ ብሎ በተለያዩ ስሞች ይጠራል፡፡ ከዚህም በመነሳት መሬት በአማራ ህይወት ውስጥ እጅግ መሰረታዊ እና ወሳኝ መሆኑን እንረዳለን፡፡ ከዚህም በመነሳት ርስት በሽህ አመቱ ለባለቤቱ ይባላል፡፡ ምንም ይሁን ምንም ርሰትህን ከሽህ አመት በኋላ ቢሆን ተከራክረህ ማስመለስ ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም ርስቱን ተቀምቶ የቀረና ያላስመለሰ በማህበረሰቡ እንደሰው ስለማይቆጠር እና ቀሪ ዘመኑን የተዋረደ ሆኖ ስለሚኖር፡፡ ርስት በሽህ አመቱ ለባለቤቱ የሚለው ብሂል በአማራ ውስጥ የመሬትን አስፈላጊነት የሚያመለክት ነው፡፡ የጨዋ ልጅና ድንች ከባድማው አይጠፋም የሚለው ንግግር ራሱ ትልቅ መልእክት ያለው ነው፡፡ ድንች መዘራት ከመጀመረ ከብዙ አመት በኋላ ድሮ ተዘርቶበት የነበረው ቦታ ላይ ከሌላ ማሳ ጋር ይበቅላል፡፡ እናም ዘሩ የማይጠፋ እህል ነው፡፡ አማራም በቀጥታ የዚህን ምሳሌ ነው ለጨዋ ልጅነት መታወቂያ ያዋለው፡፡ ልክ እንደ ድንች ሁሉ የጨዋ ልጅ ከአባቱ ባድማ አይጠፋም፡፡ ከባድማ ወይም ከመሬት አለመጥፋትም የጨዋ ልጅነት ምልክት ነው፡፡ ይህም የመሬትን ላቅ ያለ ዋጋ ያመለክታል፡፡

እናም አማራ ከመሬት ጋር እጅግ የተቆራኘ ህዝብ ነው፡፡ በባህሉም በትንሽ የድንበር መገፋፋት ራሱ እርስ በእርስ ሊጨካከን የሚችል ነው፡፡ ድንበር ክቡር ናት፤ መሬት ህይዎት ናት፡፡ በሚስትና በርስት ቀልድ የለም ሲልም ለንግግር ማሳመሪያ ብቻ አይደለም፡፡ በተግባር የሚገለጽ ነው እንጅ፡፡ የመሬት ጉዳይ ቀልድ ሆኖ አያውቅም፡፡ መሬት ከጠቅላላ ህይዎቱ ጋር ስለተሳሰረ አማራና መሬትን ነጣጥሎ ማሰብ አያችልም፡፡ አማራ ያለመሬት ህይወቱን አስቧት አያውቅም፡፡ ጠቅላላ ማህበረሰባዊ መሰረቱም መሬትና በመሬት ዙሪያ የተገነባ ነው፡፡

እናሳ? እናማ ወያኔ የዚህን ህዝብ ከመሬት ጋር በጥብቁ የተቆራኘ ትስስር ለማጥፋት እና ለማዳከም ቆርጦ ተነሳ፡፡ የአማራ ማንነቱ የተሳሰረው እና ሀብቱ የሚመነጨው ከመሬት ነው፡፡ ፖለቲካዊ፤ ምጣኔ ሀብታዊ እና ማህበራዊ መሰረቱ መሬት ነው፡፡ ወያኔም መሬትና የአማራን መሰረቶች ለመናድ መፍጨርጨሩን ተያያዘው፡፡ ብዙ ጊዜ ይገርመኝ የነበረው ነገር መለስ አገር ማለት ህዝብ እንጅ መሬት አይደለም የሚለው ለበጣ ነበር፡፡ ፊት ለፊት አግኝቶ የሚያወራው ወሬ ፍሬ ከርስኪ መሆኑን መንገር ነበር እያልኩ ስመኝ ነበር፡፡ መሬት አገር አይደለም፤ አገር ማለት ህዝብ ነው ብሎ ሲያላግጥ እሱን ተከትለው የሚነፍሱ ሰዎች ብዙ ጊዜ አይቻለሁ፡፡ የተከራከርኳቸውም አሉ፡፡ ግን እደትልቅ መገለጥ ቆጥረውት ከመደጋገም እና ከመደነቅ ውጭ ምን ማለት ነው ብለው ሲያስቡት አላየኋቸውም፡፡

ግን የመለስና የወያኔዎች መሬት ሳይሆን አገር ህዝብ ነው የሚል ስላቅ በመሰረቱ የዜሮ ብዜት ነው፡፡ መጀመሪያ የተፈጠረው መሬት ነው፤ ሰውም፡ መለስን ጨምሮ፡ ከአፈር ነው የተፈጠረው፡፡ መሬት ሳይረግጥ አየር ላይ የሚኖር የለም፡፡ ስለሰው ለማውራት መጀመሪያ ማረፊያ ቦታ ያስፈልጋል፡፡ ምንም እንኳ ከሰው ቀድሞ የተፈጠረው መሬት ቢሆንም አንዱን ከአንዱ ማበላለጥ አያስፈልግም ነበር፡፡ በእርግጥ መሬት ያለ ሰው ሊኖር ይችላል፤ ሰው ግን ያለመሬት አይኖርም፡፡ ሰው ይኖር ዘንድ መሬት የግድ አስፈላጊ ነው፡፡ መሬት ይኖር ዘንድ ግን ሰው አስፈላጊ አይደለም፡፡ በዚህም እሳቤ ሰው የመሬት ጥገኛ ነው እንላለን፡፡ የመለስ ፍልስፍናም እዚህ ላይ እርቃኗን ቆማ ትታይ እና ማሰብ በሚችል አእምሮ ውስጥ ትከስማለች፡፡

መለስ ግን መሬት ሳይሆን አገር ማለት ህዝብ ነው ሲል በእርግጥ ህዝብ እየወደደ እንዳልሆነ ይታወቃል፡፡ እሱ በውስጡ የሚወደው መሬትን ነው፡፡ መሬት ላይ ገንዘብ ይታፈሳል፡፡ ኪስና ሆድም ይሞላል፡፡ በዚህ በኩል ወገኖቹን የሌላ ብሔረሰቦች መሬት በማደልና በመሸጥ ኪሳቸውን ይሞላል፤ በዛ በኩል መሬት እኮ ምንም ማለት አይደለም ይላል፡፡ ቅድሚያ ህዝብ እያለ ያላግጣል፡፡ መሬት ህዝብ ካልሆነ ታዲያ የወሎን፤ የጎንደርን መሬት ህዝቡን እየጨፈጨፉ መውሰድ ለምን አስፈለገ? የጋምቤላን እና ጉምዝን መሬት መዝረፍ ለምን አስፈለገ? ከጎንደርና ወሎ መሬትና ህዝብ መሬት በልጦ ነው ህዝቡ የተጨፈጨፈው እግዲህ፡፡ ይህንን ግን ገልብጠው መሬት ለምኔ ህዝብ እንጅ እያሉ ያላግጣሉ፡፡ እዚህ ጋር አንድ ታሪክ ታወሰኝ፡፡ መለስ ለብቻው ይኖርበት የነበረውን እና አሁን ወያኔዎች በቡድን የሚኖሩበትን የዳግማዊ ምኒልክ ቤተመግስት የአያቴ ይዞታ ነው ይመለስልኝ ብሎ የሚከራከር ሰው እንዳለ ሰምቻለሁ፡፡ ታዲያ በቤተ መንግስት አጠገብ ባለፍኩ ቁጥር ትዝ የሚለኝ ያ ግፉአን ሰው ነው፡፡ መለስ ግን ተራራና ወንዝ፤ ሜዳና ሸለቆ አልፈልግም ብሎ ሲያበቃ ምናለብት የዚህን ሰውየ መሬት ቢመልስለት እላለሁ፡፡ የሰው ጉብታ ላይ ተጎልቶ መሬት ምን ያደርጋል ህዝብ ነው እንጅ እያለ ያላግጣል፡፡

ወያኔዎች መሬትን የጠሉበት እንግዲህ ከአማራ ጋር በተያያዘ ነው፡፡ ትግል ሲጀምሩ አማራ ብዙ መሬት ይዟል፤ ፊውዳል ነው፤ የመሬት ከበርቴ ነው ብለው ነው፡፡ ስለዚህ አማራ መጥፋት አለበት ብለው ሲደነግጉ የአማራ ሀብት የሆነውን መሬት ሁሉ ጨምረው ነው፡፡ መሬት ለአማራ የኩራቱ ምንጭ ነው፡፡ ስለዚህ የመሬትን አፋዊ ዋጋ በማኮሰስ የአማራን ኩራት መግደል አስፈላጊ ሆኖ ተገኘ፡፡ ከመሬቱ ጋር ጥብቅ ቁርኝት ስላለውም አማራን የማጥፋቱ ሂደት ከባድ ሆነ፡፡ ስሆነም እየደጋገሙ መሬት ዋጋ እንደሌለው፤ አገር ማለት ህዝብ እንደሆነ በመለፈፍ አማራውን ከመሬቱ ጋር የስነልቡና ፍች እንዲያደርግ ጣሩ፡፡ አማራው ስለመሬት ያለው ጠንካራ ግንዛቤና ትስስር ከላላ በቀላ ማፈናቀልና ያንን መሬት መውረስ ይቻላል፡፡ ልክ በጎንደርና ወሎ እንደሚያደርጉት፡፡ መሬት አያስፈልግህም፤ አንተ ብቻ ኑር ይልህና ቀና ስትል መሬትህን ወስዶ አንተን ዘበኛ አድርጎሀል፡፡ ይህች ናት የመለስ ህዝብ ማት፡፡ ይህች ናት የወያኔ ህዝብ ማለት፡፡
መለክ ሐራ