JULY 24, 2017

የኢትዮጵያ ገቢዎች እና ጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ከበደ ጫኔ ለሪፖርተር ጋዜጣ የሰጡት መግለጫ ተሳስቶ የቀረበ መሆኑንን በመጥቀስ በቀን ገቢ ግምት ላይ የተቀየረ ነገር እንደሌለ አስታወቁ። ዜናው ከመስተባበሉ በፊት የኦሮሚያ ሚዲያ ኔትዎርክ ውስጥ አዋቂዎች እንደነገሩት በመጥቀስ አቶ ከበደ ጫኔ ” አንስተኛ ነጋዴዎች ያመኑበትን ይክፈሉ ብለዋል” መባሉን ተከትሎ ክፉኛ መገምገማቸውን ጠቁሞ ነበር።

አቶ ከበደ ለቪኦኤ እንዳሉት ሪፖርተር ጋዜጣ አነጋግሯቸው ነበር። ይሁንና አሳስቶ ዜናውን አትሟል። በዚሁም ጉዳይ ከሪፖረትር ዝግጅት ክፍል ጋር ተነጋግረው ማስተካከያ እንደሚወጣላቸውና ይቅርታ እንደሚጠየቁ አስታውቀዋል። እሳቸው ይህንን ቢሉም ሪፖርተር ካነጋገራቸው እንዲህ አይነት የዜና መፋለስ ሊከሰት አንደማይችል ግምት የሰጡ አሉ። እነዚህ ክፍሎች እንዳሉት  ምንአልባትም መጠነኛ ግድፈት ሊከሰት ይችል እንደሆን እንጂ ሙሉ ዜና ሊፋለስ ስለማይችል ሚኒስትሩ ለማስተባበል ያስገደዳቸው ጉዳይ ስለመኖሩ አመላካች ነው።

ዜናው የወቅቱ ትኩስ ጉዳይ በመሆኑ መረጃው በስፋት የተስፋፋ መሆኑን ተከትሎ የመንግስት ሚዲያዎች ማስተባበያ ሰጥተዋል። በማስተባበያ ዜናው የተባለው ” ግብር ከፋዮች ያመኑበትን ይከፍላሉ” መባሉን ” ወሬ” በማለት ነው። ” በዝቅተኛ የስራ ንግድ ላይ ግብር ከፋዮች ያመኑበትን ይክፈሉ ተብሏል በሚል ሲናፈስ የነበረው መረጃም ፍፁም ከእውነት የራቀ ነው” ሲሉ አቶ ከበደ መናገራቸውን ነው ፋና የዘገበው።  የፋናን ሙሉ ዘገባ ከታች ያንብቡ። ማስተባበያውን የዘገበው ቪኦኤም አቶ ከበደን ያሰማቸው የሪፖርተር ዜና የተዛባ መሆኑንን ሲናገሩ እንጂ ከጉዳዩ ትልቅነትና ስፋት አንጻር ተያያዥ ጥያቄዎችን ለሚኒስትሩ አላቀረበም። ወይም ከቃለ መጠይቃቸው ላይ የተቆነጠረ ስለመሆኑ አልተገለጸም። በዜናው መደበላለቅ ጉዳዩ የሚመለከታቸው የደረጃ ሕ ግብር ከፋዮች እንደተምታታባቸው ለማወቅ ተችሏል።

አቶ ጁሃር መሃመድ የሚመሩት የኦሮሚያ ሚዲያ ኔት ዎርክ ከግብር ውስኔው ጋር በተያያዘ የተቀሰቅሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ሲያውጅ አቶ ከበደ ቀደም ሲል አነስተኛ ነጋዴዎች ያመኑበትን እንዲከፍሉ ማለታቸውን ተከትሎ ክፉኛ መገምገማቸውንና መተቸታቸውን ከውስጥ አዋቂዎች መስማቱን ጠቁሞ ነበር።

ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው ግብር ከፋዮች ያመኑበትን ይከፍላሉ በሚል የተናፈሰው መረጃ ሀሰት ነው – አቶ ከበደ ጫኔ

                                                                                                                                                                                                                          

በቀን ገቢ ግምቱ ላይ ቅሬታ ያለው ማንኛውም የደረጃ ሐ ግብር ከፋይ አሳማኝ መረጃ ይዞ እስከመጣ ድረስ ተገቢ ምላሽ ይሰጠዋል አለ የኢትዮጵያ ገቢዎች እና ጉምሩክ ባለስልጣን። የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ ከበደ ጫኔ ማምሻውን በሰጡት መግለጫ፥ በህጋዊ መንገድ ቅሬታን ማቅረብ እየተቻለ ሌላ ህገወጥ ድርጊት መፈፀም በህግ ያስጠይቃል ብለዋል።

በአዲስ አበባ 148 ሺህ የደረጃ “ሐ” ግብር ከፋዮች የቀን ገቢ ግምት ተከናውኖላቸዋል።

በእለት ገቢ ግምቱ በገማቾች እና ነጋዴዎች መካከል የመረጃ ልውውጥ ችግር ነበር ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፥ በአብዛኛው የቀን ገቢ ግመታው ትክክል መሆኑን ገልፀዋል። 68 በመቶ የሚሆኑ የእለት ገቢያቸው የተገመተላቸው ሰዎች ትክክል መሆኑን አምነውበት ግብራቸውን መክፈል ጀምረዋል፤ 32 በመቶ የሚሆኑት ደግሞ ቅሬታ አቅርበዋል ብለዋል።

በአጠቃላይ 23 ሺህ ቅሬታዎች ቀርበው የ20ሺዎቹ የመጀመሪያው ግምት ፀድቆ መክፈል እንዳለባቸው ተወስኗል ነው ያሉት አቶ ከበደ። በአጠቃላይ ከደረጃ “ሐ” የቀን ገቢ ግመታ ጋር ተያይዞ አሁንም የሚቀርቡ ቅሬታዎች ካሉ ባለስልጣኑ ለመፍታት ዝግጁ መሆኑንም አንስተዋል።

የደረጃ “ሀ” እና “ለ” ግብር ከፋዮች ግን የሂሳብ መዝገብ እና ካሽ ሪጂስተር ስላላቸው የእለት ገቢ ግምቱ አይመለከታቸውም ነው ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ። ዛሬ ማለዳ በአዲስ አበባ መርካቶ ነጋዴዎች ሱቆቻቸውን እንዳይከፍቱ ቅስቀሳ ሲደረግ እንደነበርና የተወሰኑ ሱቆች እስከ እኩለ ቀን ድረስ ተዘግተው መቆየታቸውን ነው ያነሱት አቶ ከበደ

ከአክሲዮን ማህበራት ጋር በተደረገ ውይይትም ነጋዴዎቹ በራሳቸው ተነሳሽነት ሳይሆን የቅስቀሳ ወረቀት እና የተለያዩ የስለት መሳሪያዎችን ይዘው የሚንቀሳቀሱ አካላት ዛቻ ምክንያት ሱቆቻቸውን ሊዘጉ መቻላቸውን አረጋግጠናል ብለዋል። ከነጋዴዎቹ ማህበራት ጋር ከተደረገው ውይይት በኋላ መርካቶ በእኩለ ቀን ወደ መደበኛ እንቅስቃሴዋ መመለሷንም አንስተዋል።

በስፍራው ነጋዴዎችን ሱቆቻቸውን እንዲዘጉ በሃይል ሲያስፈራሩ ከነበሩ ሶስት ግለሰቦች ውስጥም ሁለቱ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ዋና ዳይሬክተሩ ተናግረዋል። በሌላ በኩል በዝቅተኛ የስራ ንግድ ላይ ግብር ከፋዮች ያመኑበትን ይክፈሉ ተብሏል በሚል ሲናፈስ የነበረው መረጃም ፍፁም ከእውነት የራቀ መሆኑንም ነው አቶ ከበደ ያነሱት።

ፋና ብሮድካስት