Sunday, 06 August 2017 00:00

አለማየሁ አንበሴ

አዋጁን ተግባራዊ ያላደረገ ድርጅቱ ይታሸግበታል

‹‹የክልሉን ቋንቋ ለማሳደግ አስተዋፅኦ ያበረክታል››

1983 .ም ጀምሮ የስራ ቋንቋውን ትግርኛ ያደረገው የትግራይ ክልላዊ መንግስት፤ ማንኛውም የንግድ ማስታወቂያ ታፔላና የግድግዳ ላይ ማስታወቂያ መልዕክቶች በትግርኛ ቋንቋ እንዲፃፉ የሚያዝ አስገዳጅ አዋጅ ሰሞኑን አፀድቆ በስራ ላይ መዋል መጀመሩ ተገለፀ፡፡


አዋጁን እንዲያስፈፅም ኃላፊነት የተሰጠው የክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ አቶ ዳዊት ኃይሉ ለአዲስ አድማስ በሰጡት ማብራሪያ፤ አዋጁ ማንኛውም የንግድ ድርጅትም ሆነ አገልግሎት ሰጪ ተቋም፤ የውጪ ተሰቃይ ማስታወቂያውን ወደ ትግርኛ እንዲለውጥ የሚያስገድድ መሆኑን ጠቁመው፤ አዋጁን ተግባራዊ ያላደረገ ድርጅቱ እንደሚታሸግበት ያሳስባል ብለዋል፡፡

 ቀደም ሲል እንዲህ ያለው አስገዳጅ ህግ ባለመኖሩ፣ በክልሉ ከተሞች የሚሰቀሉ የግድግዳ ላይ ማስታወቂያዎችና ታፔላዎች የተዘበራረቀ ቋንቋ ይጠቀሙ እንደነበር የጠቀሱት አቶ ዳዊት፤ ይህን የሚያስቀር አዋጅ መፅደቁ ለክልሉ ቋንቋዎች እድገት አስተዋፅኦ ያበረክታል ብለዋል። በክልሉ የራሳቸውን ቋንቋ የመጠቀም ህጋዊ መብት የተሰጣቸው የሳኦና የኩናማ ብሄረሰቦችም በከተማቸውና አካባቢያቸው፣ ማናቸውም የግድግዳ ላይ ማስታወቂያዎችና ታፔላዎች በየራሳቸው ቋንቋ እንዲፃፉ አዋጁ ያስገድዳል ተብሏል፡፡

 አዋጁ ገና በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ እንዳልወጣ የተጠቆመ ሲሆን የመቀሌ ከተማ አብዛኞቹ የንግድ ቤቶችና ተቋማት አዋጁ መውጣቱን ተከትሎ ታፔላቸውን ወደ ትግርኛ ቋንቋ በመቀየር ተጠምደው መሰንበታቸውን ከአካባቢው ምንጮቻችን ለማወቅ ተችሏል፡፡ የቢሮ ኃላፊው አቶ ዳዊት በበኩላቸው፤ በእርግጥም ታፔላዎች ከወዲሁ እየተቀየሩ መሆኑንና የህብረተሰቡ ተግባርም በፍቃደኝነት ላይ የተመሰረተ እንደሆነ ጠቁመው፣ ገና ወደ አስገዳጅነት አለመገባቱን አስታውቀዋል፡፡
በታፔላዎቹ ላይ ጎላ ተደርጎ ከሚቀመጠው ከትግርኛ ቀጥሎ ሌላ ማንኛውንም ቋንቋ መጠቀም እንደሚቻል አቶ ዳዊት አክለው ገልፀዋል፡፡

አዲስ አድማስ