August 7, 2017

05 Aug, 2017 By ታምሩ ጽጌ \

በኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን በመንግሥት የተሰጡ መብቶች ማስፈጸሚያ ንዑስ የሥራ ሒደት ምክትል ዋና ዳይሬክተር፣ ከአገር ሊወጡ ሲሉ በቁጥጥር ሥር ዋሉ፡፡

የቀድሞዋ ምክትል ዳይሬክተር ወ/ሮ ዓለምፀሐይ ግርማይ በቁጥጥር ሥር የዋሉት፣ በመንግሥት ላይ ከዘጠኝ ሚሊዮን ብር በላይ ጉዳት አድርሰዋል ተብለው ተጠርጥረው መሆኑን የፌዴራል ፖሊስ መርማሪ ቡድን አስታውቋል፡፡

ተጠርጣሪዋ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሆነው ሲሠሩ ለተለያዩ ድርጅቶች ከቀረጥ ነፃ እንዲያስገቡ ከተፈቀዳላቸው በላይ እንዲያስገቡ መፍቀዳቸውን፣ መርማሪ ፖሊስ ለፍርድ ቤት አስረድቷል፡፡

ከተፈቀደው በላይ ከገቢ ዕቃዎች መንግሥት ከቀረጥ ገቢ ማግኘት ይገባው የነበረውን 9,099,328 ብር እንዲያወጣ ማድረጋቸውንም ለፍርድ ቤት አስረድቷል፡፡ ግለሰቧ በተጠረጠሩበት ጉዳይ ፖሊስ በማጣራት ላይ እያለ፣ ከአገር ሊወጡ ሲሉ በቁጥጥር ሥር እንደዋሉም አስረድቷል፡፡

መርማሪ ፖሊስ የተለያዩ የሰነድ ማስረጃዎችን ከተለያዩ መሥሪያ ቤቶች መሰብሰቡንና ለኦዲት ማቅረቡን፣ የኦዲተሮችን የምስክርነት በቃል መቀበሉንም አስረድቷል፡፡ የተጠርጣሪዋን ቃል መቀበል፣ የምስክሮችን ቃል መቀበልና ሌሎች ሥራዎችን በማከናወን ለዓቃቤ ሕግ ማስረከብ እንደሚቀረው በመግለጽ፣ 14 ቀናት የምርመራ ጊዜ እንዲፈቀድለት ጠይቆ ፍርድ ቤት ፈቅዶለታል፡፡

ethiopianreporter.com…