Wednesday, 09 August 2017 12:42

የብሔራዊ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆን በበልግ አብቃይና አርብቶ አደር አካባቢዎች ከግንቦት 15 እስከ ሰኔ 15 ቀን 2009 ዓ.ም ድረስ ባደረገው የምግብ ዋስትና ጥናት 8 ነጥብ 5 ሚሊየን ሕዝብ የዕለት ምግብ ዕርዳታ እንደሚያስፈልገው አረጋገጠ።

በጥናቱ የወቅቱ የዝናብ ሁኔታ፣ የእርሻ ስራ እንቅስቃሴ፣ በማሳ ላይ ያለው የሰብል ሁኔታ፤ የምርት ግምት፣ የግጦሽ እና የውሃ አቅርቦት፣ የእንስሳት አቋም እና የምርት ሁኔታ፣ የሰው እና የእንስሳት ጤና እንዲሁም በወቅቱ እየተሰራጨ ያለው የምግብና ምግብ ነክ ያልሆኑ እርዳታዎች የስርጭት ሁኔታ በመዳሰስ የማኅበረሰቡን የምግብ ዋስትና ሁኔታ ለመገምገም የተቻለ ሲሆን፤ በተገኘው ውጤት ቀደም ሲል 7 ነጥብ 8 ሚሊዮን ከነበረው የተረጂ ቁጥር ወደ 8 ነጥብ 5 ሚሊዮን ከፍ በማለት ለቀጣይ 5 ወራት ማለትም ከነሐሴ 2009 ዓ.ም እስከ ታህሳስ 2010 ዓ.ም የምግብ እርዳታ የሚያስፈልገው መሆኑ በጥናቱ ተረጋግጧል።

ይኸው የዳሰሳ ጥናት ሰብል አብቃይ እና አርብቶ አደር በሆኑት አካባቢዎች የተከናወነ ሲሆን፤ በዘንድሮው ዓመት የተረጂው ቁጥር የጨመረባቸው ምክንያቶች የበልግ ዝናብ መዛባት፣ የመኖና ግጦሽ ማነስ እንዲሁም በአንዳንድ አካቢዎችም የምርት መቀነስ እና የውሃ እጥረት መሆናቸው በጥናቱ ላይ ተመላክቷል።

በጥናቱ ላይ በብሔራዊ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አስተባባሪነት የፌዴራል ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች፣ የክልል ሴክተር ቢሮዎች፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅቶች፣ የሁለትዮሽ ስምምነት ያላቸውና ዓለም አቀፍ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ተሳትፈዋል።

ስንደቅ