(በጌታቸው ሺፈራው)

አቃቤ ህግ የቂሊንጦ እስር ቤትን በማቃጠል፣ ንብረት ማውደምና የሰው ህይወት መጥፋት ተጠያቂ ናችሁ ተብለው ክስ የተመሰረተባቸው እነ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ የክስ መዝገብ ስር ከተከሰሱ 38 ግለሰቦች መካከል የነፃ አገልግሎት እየሰጡ የሚገኙት ጠበቆች ሊከሰሱና የጥብቅና ፈቃዳቸው ሊነጠቅ እንደሚችል አስፈራርቷል፡፡ ጠበቆቹ ፍርድ ቤቱን በማስፈቀድና በማሳወቅ በእነ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ የክስ መዝገብ ለተከሰሱት ግለሰቦች በነፃ ከመቆም በተጨማሪ ለበርካታ ተከሳሾች የቆሙትን አቶ ወንድሙ ኢብሳን በማገዝም እየተከራከሩ ቆይተዋል፡፡ ይሁንና ዛሬ ነሀሴ 4/2009 ዓ.ም በዋለው ችሎት አቃቤ ህግ ለተከሳሾች በነፃ የሚቆሙት ጠበቆች ከተከሳሾች ጋር የፈፀሙት ውል እስከሌለ ድረስ ተከሳሾችን ወክለው እንዳይቆሙ፣ የሚቆሙ ከሆነም ሊከሰሱና ፈቃዳቸውን ሊነጠቁ እንደሚችሉ ማስፈራሪያ አዘል አቤቱታ አቅርቧል፡፡ ፍርድ ቤቱ ጠበቆቹ አቃቤ ህግ ያቀረበውን አቤቱታ ተቀብለው ለተከሳሾቹ የጥብቅና አገልግሎት መስጠት እንዲያቆሙ ወይንም ለጥያቄው መልስ እንዲሰጡበት ምርጫ ባቀረበው መሰረት ጠበቆቹ መልስ በመሰጠት ተከሳሾቹን ወክለው እንዲቆሙ ፍርድ ቤቱን ጠይቀዋል፡፡

ጠበቆቹ በአንድ ወንጀል የተከሰሰ ሰው የጥብቅና አገልግሎት የማግኘት መብት እንዳለው፣ እንዲሁም በአመት ቢያንስ 40 ሰዓት በነፃ የማገልግል ግዴታ እንዳለባቸው ገልፀው በነፃ የሚሰጥ አገልግሎትም ውል ሊፈፀምበትና ለፍርድ ቤትም ሊቀርብ እንደማይችል አሳውቀዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ አንድ ጠበቃ ሊጠየቅ የሚችለው የሙያ ፈቃዱን እንጅ በነፃ በቆመበት ጉዳይ ውል መጠየቅ እንደማይገባ ለፍርድ ቤቱ አመልክተዋል፡፡ በሌላ በኩል ክሱ አንድ በመሆኑና አንድ ምስክር በርካታ ተከሳሾች ላይና ተፈፀመ የሚባለው ጉዳይ ላይ እየመሰከረ ባለበት ሁኔታ ጠበቆች ደንበኛቸው ባይሆንም ሌላ ደንበኛ ላይ የተመሰከረውን ጉዳይ ላይም በመከራከር ክሱን ውድቅ ማድረግ ስላለባቸው ሌሎች ተከሳሾች በማገዝ መከራከር እንዳለባቸው ገልፀዋል፡፡ ጠበቆቹ አቶ ወንድሙ ሌላ ችሎት ለሚቀርቡ ደንበኞቻቸው ሲቆሙ፣ እንዲሁም ጠበቃ የሌላቸውን ሲወክሉ ፍርድ ቤቱ አውቆና ፈቅዶ መሆኑን በመግለፅ አቃቤ ህግ ያቀረበውን አቤቱታና ማስፈራሪያ ላይ ጠንካራ ተቃውሞ አቅርበዋል፡፡

አቃቤ ህግ ያቀረበው አቤቱታና ማስፈራሪያ የህግም የሞራል ድጋፍ የለውም ያሉት ጠበቆቹ ‹‹አቃቤ ህግ ጠበቆችን በማስፈራራትና በመክሰስ ከፍርድ ስርዓቱ ለማራቅ እየጣረ ነው›› ብለዋል፡፡ የእነ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ የምስክር ሂደት ጠንካራና የአቃቤ ህግን ክስ የሚያስተባብል ክርክር እየተደረገበት ያለ በመሆኑ እና አቃቤ ህግ ደግሞ ጠበቆችን በማራቅ ክሱ እራሱ በፈለገው መንገድ እንዲሄድለት በመፈለጉ አቤቱታና ማስፈራሪያውን እንዳቀረበ ስማቸው እንዳይገለፅ የፈለጉ ጠበቃ ገልፀዋል፡፡ አቃቤ ህግ አቤቱታና ማስፈራሪያውን ካቀረበ እና ጠበቆችም ምላሽ ከሰጡ በኋላ የፍርድ ቤቱን ብይን ሳይጠይቅ ‹‹በህጉ መሰረት አቤቱታችን አቀረብን እንጅ አላስፈራራንም›› ብሏል፡፡ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ጉዳዩን መርምሮ ለመበየን ጊዜ የሚወስድ መሆኑንና ችሎት ላይ መበየን እንደማይቻል ገልፆ፣ በገንዘብ ጠበቃ ማቆም ላልቻሉ ተከሳሾች በነፃ የሚቆሙና አቶ ወንድሙ ኢብሳን የሚያግዙ ጠበቆች ውል ሳይኖራቸው ሊቆሙ ይገባል አይገባም የሚለውን ለመበየን በአዳር ቀጠሮ ይዟል፡፡