August 16, 2017 05:17

አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከተነሳ ሁለት ሳምንት ሳይሞላው ለሁለተኛ ጊዜ በባህር ዳር ከተማ ቦምብ በማፈንዳት የተጠረጠሩ ግለሰቦች፣ ጫካ ውስጥ ሲንቀሳቀሱ መያዛቸውን የከተማው ፖሊስ መምርያ አስታወቀ፡፡

የመምርያው ኃላፊ ኮማንደር ዋለልኝ ዳኘው ማክሰኞ ነሐሴ 9 ቀን 2009 .. ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ ቅዳሜ ምሽት በባህር ዳር ከተማ ቀበሌ 04 በተለምዶ ብሔራዊ ሎተሪ ቅርንጫፍ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ቦምብ በማፈንዳት የተጠረጠሩ ወጣቶች ወደ ትውልድ ቦታቸው ጎንደር ለማምለጥ ጫካ ውስጥ ሲንቀሳቀሱ ተይዘዋል፡፡

ፍንዳታው በተከሰተበት ወቅት ተጠርጣሪ መያዝ እንዳልተቻለ የጠቆሙት ኃላፊው፣ በሒደት በተደረገው ጥረትና በኅብረተሰቡ ድጋፍ ሦስት ተጠርጣሪዎች መያዛቸውን ገልጸዋል፡፡ አንደኛው ቦምብ ገዝቶ ለአፈንጂዎች እንደሰጠ የተጠረጠረ ሲሆን፣ ሁለቱ ደግሞ ከድርጊቱ ጋር ተሳትፈዋል ተብለው የተጠረጠሩ መሆናቸውን አክለዋል፡፡

ተጠርጣሪዎቹ ድርጊቱ በተከሰተ በሁለተኛው ቀን ሰኞ ነሐሴ 8 ቀን 2009 .. መያዛቸውን ጠቁመው፣ ባህር ዳር ውስጥ በመንግሥት ሥራ ላይ እንደነበሩ አስረድተዋል፡፡ ሁለቱ የትውልድ ቦታቸው ደቡብ ጎንደር ዞን ውስጥ መሆኑንና ወደዚያ ሄደው ለማምለጥ ሲሉ መያዛቸውን ገልጸዋል፡፡

እነዚህ ሦስት ተጠርጣሪዎች አፈነዱት በተባለው ቦምብ በሁለት ወጣቶች ላይ ጉዳት መድረሱን ኮማንደሩ አክለው ገልጸዋል፡፡ ጉዳት ከደረሰባቸው ወጣቶች መካከል አንደኛው የ25 ዓመት ዕድሜ እንዳለው፣ ጉዳት የደረሰበትም ኳስ ጨዋታ ለማየት ከቤቱ ወጥቶ ሲሄድ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ሌላኛዋ ተጎጂ ደግሞ የ22 ዓመት ወጣት እንደሆነችና ከሥራ ወደ ቤቷ ስትገባ ጉዳት የደረሰባት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ሁለቱ ተጎጂዎች የባህር ዳር ከተማ ነዋሪዎች መሆናቸውን ገልጸው፣ በአሁኑ ወቅት በፈለገ ሕይወት ሆስፒታል የሕክምና ዕርዳታ እያገኙ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡

እንደ ኮማንደር ዋለልኝ ገለጻ፣ ሁለት ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በባህር ዳር ከተማ ሁለት የቦምብ ፍንዳታዎች አጋጥመዋል፡፡ በዚህ ሳምንት ውስጥ ሌሎች ተጨማሪ ሊፈነዱ ተዘጋጅተው የነበሩ ሁለት ቦምቦችን ማምከን መቻሉንም ተናግረዋል፡፡

‹‹ይህ ችግር ሊፈጠር የቻለው ፀረ ሰላም ኃይሎች በከተማዋ ውስጥ ያሉ ወጣቶችን በማታለልና ገንዘብ በመስጠታቸው ነው፤›› ብለዋል፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በተነሳ ማግሥት የአማራ ክልል መዲና በሆነችው ባህር ዳር ባለፈው ዓመት የሞቱ ዜጎችን ለማሰብ በተካሄደው ተቃውሞ ጋር በተያያዘ፣  የተለያዩ ሰዎች ስለመታሰራቸው መዘገባችን ይታወሳል፡፡

By ሳተናው