ትግራይ ክልልና አዲስ አበባ በመንገድ ልማት ቀዳሚዎች ሲሆን የአማራ ክልል ግን መጨረሻ እንደሆነ በቅርቡ የወጣው የአለም ባንክ ሪፓርት አስታወቀ።

በ10 ዓመታት ውስጥ (ከ2006-2016 እኤአ) ያለውን የመንገዶች ስርጭት ላይ በተደረገ ጥናት በትግራይ ክልልና በአዲስ አበባና በዙሪያዋ ባሉ የኦሮምያ ክልል ከተሞች የመንገድ ስርጭት ከፍተኛ ሲሆን፥ በአማራ ክልልና በገጠሪቱ የኢትዮጵያ ክፍል ደግሞ አነስተኛ የመንገድ ትስስርና ልማት መኖሩን የአለም ባንክ ጥናት ያመላክታል። ጥናቱ እንዳመለከተው የኢንቨስትመንትና ሌሎች መሰረተ-ልማቶች ስርጭትም እንደመንገዱ ሁሉ በአዲስ አበባና በትግራይ ቀዳሚ ሲሆን በአማራ ክልል ግን ኋላ ቀር ነው።

የአሜሪካ ብሄራዊ የውቂያኖስና የከበባቢ አየር አስተዳደር የሚታዩ ሞገዶችን በመጠቀም በሳተላይት ምልከታ ባደረገው ጥናት በጠቅላላውም ሆነ በጨለማ ግዜ አማካኝ የመቀሌ ከተማ ብርሃማነት ከፍተኛ ሲሆን (የመብራት ስርጭቷ ከፍተኛ እንደሆነ ይጠቁማል) ጎንደር ከተማ ግን በጠቅላላውም ሆነ በማታ ግዜ ባላት አማካኝ ብርሃናማነት መጨረሻ ናት።

በአለም ባንክ ስር ፕሪያንካ ካንትና በሚካኤል ጊገር ተሰርቶ መስከረም 11 ቀን 2010 ዓ\ም ይፋ የሆነው ይህ ሪፓርት እንደሚያሳየው ከመንገድ ልማት መስፋፋት ጋር በተያያዘ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች ትኩረት በማዕከላዊ ኢትዮጵያና በሰሜን ኢትዮጵያ ከፍተኛ ነው።

ከሳተላይት በሚታይ ምስል ሩቅና በኢኮኖሚ ኋላ ቀር የሆኑ ክልሎች እንዲሁም አማራ ክልል ጨለማማ ሲሆኑ፥ የመንገድ ስርጭት፥ የሌሎች መሰረተ ልማት ስርጭትም ሆነ የኢኮኖሚ እድገት ላይ ኋላ ቀር ሲሆኑ በስርጭት ዘርፍም እኩልነትና ፍትሃዊነት እንዳልሰፈነነና እንደማይታይ ያመላክታል።

በአንዳንድ ክልሎች (አማራ ክልልንም ጨምሮ) በክልል ውስጥና ከክልል ውጭ ያለ የመንገዶች ትስስር በጣም ደካማ ሲሆን የሰው ሃይል ፍሰት፥ ሸቀጦችንና የግብርና ምርቶችን ማሰራጨት ላይ ተጽዕኖ እንዳለውና የገብያ ተደራሽነትን እንደሚገታ ጥናቱ ያመላክታል።

“በግብርናና አገልግሎት ዘርፉ ላይ በሚታዩ እድገቶች የተነሳ ሃገሪቱ የተወሰነ እድገት ማሳየት ብትችልም የኢንዱስትሪ ዘርፉን ለማሳደግ የተጀመረው ሂደት የቅርብ ግዜ ስራ ሲሆን ከአዲስ አበባ ውጭ ባሉ ሁለተኛ ከተሞች ላይ በኢንዱስትሪ ዘርፍ ያን ያህል የጎላ ለውጥ የለም ይላል ጥናቱ። ወደ አዲስ አበባ ያለው ከፍተኛ የሆነ የሰው ሃይል ፍሰት እንደሚያሳየውም በሁለተኛ ከተሞች ህዝቦችን ተጠቃሚ ሊታደርግ የሚችል ለውጥ ያን ያህል እንዳልሆነ ነው” ይላል ሪፓርቱ።

Source: Branna Radio