Wednesday, 11 October 2017 12:35  

በ 

የሱዳን መንግስት ዓለም አቀፍ ሽብርተኝነትን ይደግፋል እንደዚሁም በዜጎቹ ላይ የሰብአዊ መብት ጥሰትን ይፈፅማል በሚል አሜሪካ የኢኮኖሚ ማዕቀብ ከጣለችበት ሁለት አስርት ዓመታት የተቆጠሩ ሲሆኑ ይህ ማዕቀብ ከሰሞኑ የተነሳ መሆኑን የሰሞኑ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ዘገባዎች ያመለክታሉ። ሱዳን የመጀመሪያው ማዕቀብ የተጣለባት እ.ኤ.አ በ1997 ሲሆን ይህም ማዕቀብ የንግድ ማዕቀብን እንደዚሁም በውጭ ባንኮች የሚገኙትን የሀገሪቱን ገንዘብ እንዳይንቀሳቀስ እገዳ ማድረግ ያካተተ ነበር።

ይህንን ማዕቀብ ተከትሎ የሀገሪቱ ኢኮኖሚ ክፉኛ የተንኮታኮተ ሲሆን የሱዳን መንግስት ማዕቀቡ እንዲነሳለት በተደጋጋሚ ተማፅዕኖ ሲያሰማ ቆይቷል። ፕሬዝዳንት ኦባማ በኢትዮጵያ በነበራቸው ጉብኝት በአፍሪካ ህብረት ዲፕሎማቶች በኩል የተማፅዕኖ ደብዳቤው እንዲደርሳቸው ጥረት ተደርጓል። ፕሬዝዳንት ኦባማ ሁኔታውን በመገምገም በሱዳን ላይ የተጣለው ማዕቀብ በመጠኑ እንዲላላ ማድረግ ቢችሉም ማዕቀቡ እንዲነሳ ያደረጉበት ሁኔታ አልነበረም። ሱዳን በተለይ በፋይናንስ ዘርፉ የተጣለባት ማዕቀብ የውጭ ባለሀብቶች መዋዕለ ነዋያቸውን በሀገሪቱ እንዳያፈሱ ከማድረግ ባሻገር ያሉትም አምራች ኩባንያዎች ሳይቀሩ በምርት ግብዓቶች እጥረትና በመለዋወጫ ችግር ምክንያት ሥራቸውን ሳይቀር ሙሉ በሙሉ እንዲያቋርጡ እስከማድረግ ደርሷል። ቦይንግና ሌሎች አውሮፕላን አምራች ኩባንያዎች ከሱዳን አየር መንገድ ጋር የነበራቸውን ግንኙነት በማቋረጣቸው ሱዳን ኤርዌስ ከገበያ ውጪ ለመሆን ተገዷል።

እንደ አልጀዚራ ዘገባ ከሆነ አሁን የተነሳው የኢኮኖሚ ማዕቀብ የሱዳን ኢኮኖሚ እንዲነቃቃ በማድረጉ ረገድ ከፍተኛ ሚና ይኖረዋል። ዘገባው የአሜሪካ ስቴት ዲፓርትመንት ቃል አቀባይ ሄዘር ኑሬትን ዋቢ በማድረግ እንደጠቀሰው ከሆነ ሂደቱን እዚህ ደረጃ ለማድረስ 16 ወራትን የፈጀ የዲፕሎማሲ ስራን ጠይቋል።