Obbo Mulaatuu Gammachuu miidiyaaleef ibsa yoo kennan

የኢትዮጵያ መንግሥትም ሆነ ገዥው ፓርቲ ለሕዝቡ ጥያቄ ምላሽ እየሰጠ እንዳልሆነ የኦሮሞ ፌዴራሊሰት ኮንግረስ ዛሬ በሰጠው መግለጫ አሳወቀ።

ሰሞኑን እየተደረጉ ባሉት የተቃዉሞ ሰልፎች የሰው ሕይወት መጥፋቱና ንብረት መውደሙ አሳስቦኛል ያለው ኮንግረሱ መንግሥት ለሕዝቡ ጥያቄ ትኩረት መስጠት አለበት ሲል አስታውቋል።

የፖለቲካ እስረኞች እንዲፈቱና ከመኖሪያቸው የተፈናቀሉ ዜጎች በአስቸኳይ ወደነበሩበት ተመልሰው እንዲቋቋሙ ጠይቋል።

ጨምሮም የመንግሥት ሃላፊዎችን ጨምሮ ለሰው ሕይወት መጥፋት ምክንያት የሆኑ ሰዎች ለፍርድ እንዲቀርቡ ኮንግረሱ ጠይቋል።

የፓርቲው ምክትል ሃላፊ ሙላቱ ገመቹ ሰሞኑን በተደረጉት ሰላማዊ ሰልፎች ላይ የፓርቲውን ዓርማ ይዘው የታዩት ሰዎች ፓርቲውን የማይወክሉና ሌላ ተልዕኮ ያላቸው መሆኑን ተናግረዋል።

በኦሮሚያና በኢትዮጵያ-ሱማሌ ክልሎች ድንበር አካባቢ የተከሰተው ግጭት በሕዝብ መካከል የተነሳ ሳይሆን መንግስት ሆነ ብሎ የሕዝቡን ጥያቄ ላለመመለስ ያደረገው እንደሆነ የተናገሩት አቶ ሙላቱ ጉዳዩ በታጠቁ የመንግስት ሃይሎች ሕዝብ ላይ ተደረገ ጥቃት ነው ብለዋል።

እነዚህ የታጠቁ ኃይሎች በሕዝቡ ላይ የሚያደርጉት ጥቃት በማስቆም ረገድ መንግሥት የሚጠበቅበትን ሥራ እንዳልሠራና የሕዝቡን መብት ማስከበር እየተሳነው ነው ብለዋል።

በአጠቃላይ ሰሞኑን እየተከሰቱ ያሉትን ክስተቶች ተከትሎ “ሃገር አለን ማለት እያሳሰበን ነው” ብለዋል።

በመጨረሻም የኦሮሚያ ሕዝብ በክልሉ የሚኖሩ ብሔሮችና ብሔረሰቦችን ሰላምና ደህንነት እንዲጠብቅ ጥሪ አቅርቧል።

ቢቢሲ ዜና