ቴዎድሮስ አበበ

Washington, DC ጥቅምት ፳፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም. │ November 7, 2017

 

በዓለት ላይ ታንጾ በወርቅ የተጻፈ

በሰማያዊ ክብር ጸንቶ የገዘፈ

የማይገረሰስ ዘመን የማይሽረው

የዓለም ማዕበል የማይገፈትረው

ሊጥሉት፣ ሊፍቁት፣ ሊያጠፉት ቢጥሩ

የማይነቀንቁት ከጠበቀው ስሩ

የማይደበዝዝ ነው ደምቆ የሚያበራ

የአፍሪካ ፀሐይ፣ የነፃነት አውራ

የጥቁር ሕዝብ ሰንደቅ የድል ብርሃን ተስፋ

የማንነት መብራት መቼም የማይጠፋ . . .

“ኢትዮጵያ” ስሟ ነው “ኢትዮጵያ” ዓርማችን

ሲያበራ የሚኖር መሪ ኰከባችን። “ኢትዮጵያ” ስሟ ነው አይጠፋም፣

አይወድቅም ቀደምት፣ ባለታሪክ ክብሯ አይፋቅም

በመንፈሣዊውም በዓለማዊ መዝገብ

“ኢትዮጵያ” ስሟ ነው ቀድሞ የሚታሰብ።

ስሟን ሊሰርዙ፣ ስሟን ሊያቆሽሹ

ከማንነታቸው ተጣልተው የሸሹ

ይደክማሉ እንጂ ያልታደሉ ሆነው

“ኢትዮጵያ” ተተክሏል ምንም ሀይል ላይነቅለው።

በእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ታትሟል ቀለሟ

ኢትዮጵያ “ኢትዮጵያ” ናት ይዘመራል ስሟ

. . . ኢትዮጵያ “ኢትዮጵያ” ናት፤ ገና ይነግሣል ስሟ