አጭር የምስል መግለጫሮበርት ሙጋቤ እና የዚምባብዌ ጦር አባል መግለጫ ሲያነቡ

ሮበርት ሙጋቤ በቁጥጥር ስር ውለዋል፤ ደህንነታቸውም ይጠበቃል ሲል የዛኑ ፒኤፍ ፓርቲ ይፋዊ የትዊተር ገጽ አስታውቋ። የዚምባብዌ ጦር የሃገሪቱን ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያ ከተቆጣጠረ በኋላ በሰጠው መግለጫ ”ይህ መፈንቅለ መንግሥት አይደለም። የጦሩ ተልዕኮም ወንጀለኞችን በቁጥጥር ስር ማዋል እንጂ ሙጋቤን አይደለም” ብሎ ነበር። ጦሩ ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያን ከተቆጣጠረ በኋላ ጣቢያው የትግል ሙዚቃዎችን እያጫወተ ይገኛል። በሃራሬ የምትገኘው የቢቢሲ ዘጋቢ ግን ”የጦሩ እንቅስቃሴ መፈንቅለ መንግሥት ነው የሚመስለው” ትላለች።

• ጦሩ ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያን ከተቆጣጠረ በኋላ ”መፈንቅለ መንግሥት አይደለም” ብሏል

በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የዩናይትድ ስቴትስ አምባሳደር የነበሩት ሳማንታ ፓወር ”ግሬስ ሙጋቤ የሚፈጽሙት ተግባር ነው ጦሩ ይህን አይነት እርምጃ ለመውሰድ እንዲገደድ ያደረገው” ሲሉ ተናግረዋል።

በከፍተኛ ደረጃ የታጠቁ የሃገሪቱ የጦር ኃይል አባላት በሃራሬ ጎዳናዎች ላይ ዛሬ ጠዋት በብዛት ታይተዋል። ጦሩ የሃራሬ ጎዳናዎችን የትራፊክ እንቅስቃሴ ሲመራ የሚያሳዩ ፎቶዎችም ታይተዋል።

የዚምባብዌ ጦር

ኒውስ 24 የተሰኘ የደቡብ አፍሪካ የቴሌቪዥን ጣቢያ ሮበርት ሙጋቤ ሥልጣን ለመልቀቅ ዝግጅት እያደረጉ ነው ሲል ተጨማሪ መረጃ ሳይሰጥ ዘግቧል። ሙጋቤ ምክትል ፕሬዝዳንት የነበሩትን ኤመርሰን ምናንጋግዋን ከስልጣን ካባረሩ በኋላ በዙምባብዌ የፖለቲካ ውጥረት ነግሶ ቆይቷል።

• ሙጋቤ ታማኝ አይደሉም ያሏቸውን ምክትላቸውን ከስልጣን አነሱ

ሙጋቤ ምክትላቸውን ታማኝ አይደሉም በማለት ከሥልጣን ካባረሩ በኋላ የሮበርት ሙጋቤ ባለቤት የሆኑት ግሬስ ሙጋቤ ባለቤታቸውን በመተካት ቀጣይ የዚምባብዌ መሪ ይሆናሉ ተብሎ ነበር።

ግሬስ ሙጋቤ እና ኤመርሰን ምናንጋግዋ
አጭር የምስል መግለጫግሬስ ሙጋቤ እና ኤመርሰን ምናንጋግዋ

የቀድሞው የደህንነት ሹም የነበሩት ምናንጋግዋ ፕሬዝዳንት ሙጋቤን የመተካት ተስፋ የተጣለባቸው መሪ ነበሩ። ኤመርሰን ምናንጋግዋ ከሥልጣን ከተባረሩ በኋላ ለሕይወቴ ሰግቻለው ብለው ከሃገር ሸሽተው ወጥተው ነበር።

ዛሬ እየወጡ ያሉ ሪፖርቶች እንደሚያሳዩት ከሆን ኤመርሰን ምናንጋግዋ ወደ ሃገር ተመልሰዋል።