አስገራሚ ትዝብት፡

በጌታቸው ሺፈራው

ሳተናው

By ሳተናው

November 17, 2017 04:51

“በዚህ ፍትህ በሌለበት ሀገር እንደኛ መሆን መታደል ነው። ዳኛ መሆን ከባድ ነው።……ቢገባችሁ የምንታገለው ለእናንተም ነው!” ቴዎድሮስ አስፋው

” መሳርያ ይዛችሁ የመጣችሁት ስርዓት ለማስከበር ነው። ” መሃል ዳኛው ለማረሚያ ቤቱ ፖሊስ አዛዥ

“የዘገየ ፍትህ እንደተከለከለ ይቆጠራል ያላችሁን ራሳችሁ ናችሁ” ፍሬው ተክሌ

ዛሬ ህዳር 8/2010 ዓም በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በእነ ትንሳኤ በሪሶ የክስ መዝገብ ክስ የተመሰረተባቸው 9 ተከሳሾች ይከላከሉ አይከላከሉ የሚል ብይን ለመስማት ፍርድ ቤት ቀርበው ነበር። ተከሳሾቹ በተደጋጋሚ ለብይን የተቀጠሩ ሲሆን ፍርድ ቤቱ ዳኛ ባለመሟላቱ ብይኑ እንዳልተሰራ በመግለፅ ለታህሳስ 6/2010 ዓም የአንድ ወር ቀጠሮ ሰጥቷል።

ከተከሳሾቹ መካከል ያለ ጠበቃ የሚከራከሩት ዳንኤል ተስፋዬ፣ ኤርሚያስ ፀጋዬ፣ ፍሬው ተክሌና ቴዎድሮስ አስፋው ፍርድ ቤቱ ስለሰጠው ቀጠሮ እና በማረሚያ ቤቱ ስለሚፈፀም የሕግ ጥሰት አስተያየት ለመስጠት እጃቸውን ቢያወጡም ፍርድ ቤቱ አልተቀበላቸውም። ፍርድ ቤቱ ” ከአቅማችን በላይ ነው” ብሎ እንዳይናገሩ ሲከለክል ቴዎድሮስ አስፋው ” የታሰርነው የመናገር መብታችን ለማስከበር ስንታገል ነው። አሁንም ፍርድ ቤቱ የመናገር መብታችን ሲከለክል ዝም አንልም” ብሏል። ቴዎድሮስ ይህን ሲናገር መሃል ዳኛው “ምን ልታመጣ?” ብለዋል። ቴዎድሮስ አስፋው ” በዚህ ፍትህ በሌለበት ሀገር እንደኛ (ተከሳሽ) መሆን መታደል ነው። ዳኛ መሆን ከባድ ነው። የታሰርነው የመናገር መብታችን ለማስከበር ነው። ወደፊትም እንታገላለን። ቢገባችሁ የምንታገለው ለእናንተም ነው!” ብሏል።

ከቴዎድሮስ አስፋው በተጨማሪ ፍሬው ተክሌም ቂሊንጦ እስር ቤት ለፍርድ ቤት ለማቅረብ በፅሁፍ ያቀረበውን አቤቱታ ይዞ እንዳይመጣ እንደከለከለው ገልፆ በቀጠሮውና እስር ቤት በሚፈፅመው በደል ላይ አስተያየት መከልከላቸው አግባብ እንዳልሆነ ገልፆአል። ፍሬው ተክሌ አክሎም “የዘገየ ፍትህ እንደተከለከለ ይቆጠራል ያላችሁን ራሳችሁ ናችሁ” ብሏል።

ቴዎድሮስ አስፋው፣ ፍሬው ተክሌ፣ ኤርሚያስ ፀጋዬና ዳንኤል ተስፋዬ በችሎት ቅሬታቸውን ባቀረቡበት ወቅት ፍርድ ቤቱ ፖሊስ ከችሎት እንዲያስወጣቸው ትዕዛዝ ሰጥቶ፣ በፖሊስ ከችሎት እንዲወጡ ተደርገዋል። አራቱ ወጣቶች በፖሊስ ከችሎት እንዲወጡ ሲደረጉም ቅሬታቸውን ሲናገሩ ተደምጠዋል። መሃል ዳኛው የማረሚያ ቤት ፖሊስ አዛዡን አስጠርተው ” እኛ አልተመቸንም ስንል እንደፈለጉ መጮህ የለባቸውም። መሳርያ ይዛችሁ የመጣችሁት ስርዓት ለማስከበር ነው። ” ብለዋል።

ችሎት እየተከታተሉ የነበሩት የተከሳሽ ቤተሰቦችም ቅሬታቸውን የገለፁ ሲሆን የፍሬው ተክሌ እናት “እግዚያብሄር ይፍረድ!” ብለው ከችሎት ሲወጡ በችሎት ተጠርተው ማስጠንቀቆያ ተሰጥቷቸዋል።

በእነ ትንሳኤ በሪሶ የክስ መዝገብ ስር የተከሰሱት

(ፎቶው (ከግራ ወደ ቀኝ) የኤርሚያስ ፀጋዬ፣ የፍሬው ተክሌ፣ የዳንኤል ተስፋዬ እና የቴዎድሮስ አስፋው ነው።)

  1. ትንሳኤ በሪሶ

  2. ዳንኤል ተስፋዬ

  3. ግሩም አስቀናው

  4. ቴዎድሮስ አስፋው

  5. ፍሬው ተክሌ

  6. ኤርሚያስ ፀጋዬ

  7. አሰጋ አሰፋ

  8. ጌታቸው ይርጋ

  9. ሽቴ ሙሉ እና ክሳቸው የተቋረጠላቸው ሀይሌ ማሞ ናቸው፡፡