ብዙዎቻችሁ የኔን ትችት ያነበባችሁ ስለ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም ስተች በጥንቃቄና በአክብሮት ‘በአንቱታ” ነበር (የምተቸውን ነጥብ ሳልስት ማለት ነው)። ዛሬ ግን ስደተኛውን ሁሉ በሚያስደነግጥ የስድብ ቸነፈር ገርፈውናል እና አክብሮትን የማያወቅ ሰው አንተ መባሉ ባህላችን ነውና ‘እሱ’ በሚል የአጸፋ መልስ ስምልስ ቅር የሚላችሁ ሰዎች ካላችሁ ሰውየው የጻፈውን ማንበብና ለዚህ ቁጣ እንዴት እንዳደረሰን መመዘን ነው። የፕሮፌሰሩ በስደተኛ ላይ የስድብ ናዳውን ለማንበብ “ሳተነው.ካም” ላይ የተለጠፈውን ይህንን አንብቡ-ጎሠኛነት በባዶ ሜዳ (መስፍን ወልደማርያም) http://www.satenaw.com/amharic/archives/41634
ይህ ጽሑፍ በተለጠፈባቸው ቦታዎች ልኬአለሁ፡ሆኖም እንደተለመደው ድረገፆቹ የወያኔን ባህሪ እየተከተሉ ፕሮፌሰሩን ለመከላከል ሲሉ በወገንተኛነት የኔን መልስ ካላፈኑት በስተቀር ሕዝቡ እአንዲያነብበው የመጀመሪያው ክፍል ልኬአለሁ። ሁለተኛው በትልቁ ፕሮፌሰር ማን ናቸው? የሚለውን እንደየሁኔታው ይከተላል። ሰውየው እንደዝምባቡዌው መሪ በየመቀመጫው እንደሚያንቀላፋው ሙጋቤ ባያንቀላፋም፤ ብዕሩን መቆጣጠር ያቃተው ቅዠት ውስጥ ያለ አንድ እግሩ ጉድጓድ ውስጥ የከተተ ሰውየ የስደብ ናዳውን ያወረደው በየአረብ አገሮች በባርነትና በውርደት የሚኖሩ ስለ አገራቸው መዋረድ የሚቆጫቸው ኢትዮጵያዊያን፤ በአውሮጳ ፤በሰሜን አሜካና በየአለማቱ በፋሺስቱ ወያኔ አፈሙዝ እና ግፍ ተሰድደው የሚኖሩትን በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ላይ ያወረደው “የስደብ ናዳው” ሳይበቃን “ኢትዮጵያዊነታችንን” ሰጪና ከልካይ ሆኖ ስለ አገራችን አያገባችሁም ወደ ማለት ድፍረት ተሸጋግሯል። ይህ ሰውዬ ስደተኛውን ከነልጆቻቸው ጭምር መዝለፍን የመጀመሪያ ሳይሆን ሁለተኛው ጊዜ ነው። የሚገርምው ደግሞ የራሱ ልጆችና ቤተሰቦች እዚህ አሜሪካ ውስጥ እየኖሩ ነው እኮ እኛን ሞራለ ቢሶች፤ ፈሪዎች፤ ለኩባያ ሻይ እና ለብስኩት ሃይማኖታችሁን የምትሸቱ ሲል የሰደበን!!!!! አይገርምም?

ሞራለ ቢስ እያለ የሚሰድበን ሰውዬ፤ ሞራሉን ለማሳየት መጀመሪያ ልጆቹንና የልጅ ልጆቹን ከስደት አለም ውስጥ አስወጥቶ፤ ኑ ወደ አገራችሁ ብሎ ሲያሳየንና ማስወጣት ሲችል እንጂ ልጆቹና የልጅ ልጆቹ አብረውን ተሰድደው እየኖሩ ሌላውን ሲዘልፍ ‘ሞራሉ ከየት እንዳገኘው አስገራሚ ሆኖ አግኝቼዋለሁ”። የልጆቹን በስደት መኖር የዘነጋበት ምክንያት በየመንበሩ የሚያስተኛው የሙጋቤ እንቅልፍና የመዘንጋት በሽታ ተላልፎታል ከማለት ምን ልንል ይቻለናል? ተከብሮ ከመኖር ይልቅ በስተ እርጅና ወደ ዘለፋ መግብት ምን ይባላል?

ፕሮፌሰር መስፍን እንዲህ ይላል፦ << ማንነቱን ለምቾትና ለሆዱ የለወጠ፣ የተወለደበትንና ያደገበትን ሃይማኖት በብስኩትና በሻይ የቀየረ፣ ተጨንቆና ተጠቦ በማሰብ ከውስጡ ከራሱ ምንም ሳይወጣው ሌሎች ያሸከሙትን ጭነት ብቻ እያሳየ….>> <<ኩራት እራት>> ይላል ፕሮፌሰሩ ስድብ።

አዎ ልክ ነው የፕሮፌሰሩ አባበል ጥቂት የማይባሉ ስደተኞች ምሁራንና ያልተማሩ ሰዎች በዛው በተገለጸው መገለጫ ሚገለጹ ዜጎች አሉ። ልክ ነው፡ ሆኖም ያንን ሁላችንም ጠቅልሎ የሚዘልፍ መገለጫ መግለጽ ልክ አይደለም። ፕሮፌሰሩ በጽሁፉ ድምዳሜ “ኩራት እራት” ሲል ተመጻድቋል። ለመሆኑ ማን ነው የኩራትና የውርደት ትርጉም የሚያውቀው? ባልሰራው ወንጀል ሰርቻለሁ ብሎ በፍርሃት ጫና ፈርሞ ከወያኔ እስር የወጣው ማን ነው? ምን እሚሉት ኢትዮጵያዊ ኩራት ነው ፕሮፌሰሩ የሚያወራው? <ኩራት እራት?!!>> ይህ አባባል እነ እስክንድርና እና ሌላ ጀግና ታሳሪ ዜጎች ቢለው እንጂ ‘በሺዎቹ ህጻናት ባዶ እጃቸው ብረት ከታጠቀው አጋአዚ ወታደር በመርካቶና በየአቅጣጫው እየተናነቁ በጥይት ሲወድቁ “በፍርሃት ተርበትብቶ መለስ ዜናዊ ያረቀቀውን ማዘዣ ፈርሞ ከእስር የወጣ እንደ ፕሮፌሰር መስፍን ያለ “ኩራት እራት’ የሚለውን ምሳሌ አይሄድም’። ሽማግሌዎች በፍርሃት ተርበትብተው “ባልሰሩት ወንጀል ፈርም ሲባሉ እየፈረሙ ከእስር ሲወጡ ወጣቱ ወደ ስደት ቢያመራ ፍርሃትና መበርከክን ማን ነው ያስተማረው? ተወቃሹስ ማን ነው? ሽማግሌዎችና ምሁራን በፍርሃት ከተርበተበቱ ወጣቱ ሞራሉ ከየት ያገኘዋል? ሽማግሌዎች በፋሺስቶች ፊት ፍርሃትን ካልተቋቋሙት ዜጎች በምን የመንፈስ ትጥቅ ይቋቋሙት?

ለመሆኑ ፕሮፌሰሩ በስደተኞች ላይ ያወረደው የስድብና የውርደት ናዳ ስንት ጀግና በመትረየስ በክላሽ በቦምብ እጅ ለእጅ የጨበጣ ውግያ አድርጎ፤ የእናት አገሩን ዳር ድምበር ለማስከበር የተዋደቀ፤ መከራውን ያየ ጀግና እንዳለ ያውቃል? እነዚህ ጀግኖችን ‘ፈሪዎችና አገር ሿጮች በውጭ አገር ሃይል የሚነዱ ግኡዛን እቃዎች አድርጎ መዝለፍ ምን የሚሉት ትምህርት ትችት ነው? ከአንድ ተማረ ከሚባል የዩኒቨርሲቲ-ፕሮፌሰር እንዲህ አይነት አንደበት ዘለፋ ሲወጣ ምን ይባላል? ደግሞ መቀበሪያችሁ ውጭ አድርጉ ሬሳችሁ እዚህ አገር አይገባም ይበለን? አገራችንን ለማስከበር በጦር ሜዳ የተዋጉት የተለያዩ ጀግኖችን እኮ ነው- ለተዋደቃችሁላት መሬት ኢትዮጵያ “መቀበሪያ ያላችሁም፤ እዛው አገራችሁ ውስጥ ፈረንጅ አገር ሬሳችሁ ይቀበር፤ ምናችን አይዳለችሁምና መቀበሪያችሁን ፈልጉ” እያለቸው ያለው። በጣም ይገርማል!

እጅግ የሚያበሳጨውን እባካችሁ ይህንን አንብቡልኝ፡ <<እዚያው በያገራቸው እየተነታረኩ ዕድሜያቸውን ጨርሰው መቀበሪያ ይፈልጉ፤>> ይላል ፕሮፌሰሩ።

ለዚህ መልስ ስሰጥ ወደ ንዴት ወስዶኝ የማይሆን ዘለፋ ውስጥ እንዳለገባና እንደ ፕሮፌሰሩ አንባቢን አንዳላስቀይም ልተወውና ፍርዱን ለናንተው ልተው።

በትግርኛ አንድ የምንመስለው ምሳሌ አለን፡<<ሁዉኽ ኣንጭዋ ዝደቀሰ ድሙ ይቕስቅስ>>

ትርጉም፡- <<ችኩል/ተቅበዝባዥ/ አይጥ የተኛን ድምት ይቀሰቅሳል>> ይባላል። የፕሮፌሰሩ በስደተኛው ላይ ያልተገራ የስድብ ናዳ ማውረድ በራስ ላይ ውርደት (ዲስ ሪስፔከት) መጋበዝ ነው። “ሊደርቅ ያለ ኩሬ ይሸታል” ይላሉ ትግሬዎች የጥንት አባቶች። ጌታቸው ረዳ (ኢትዮሰማይ አዘጋጅ) getachre@aol.co