BBC SOMALI

በሶማሊያ ፓርላመንት የተቋቋመው ኮሚሽን አወዛጋቢ የተባለውን የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጭ ግንባር ባለስልጣን ለኢትዮጵያ ተላልፎ መሰጠት ህገ-ወጥ መሆኑን አሳውቋል።

የኮሚሽኑ ሪፓርት እንደገለፀው የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጭ ግንባር የአሸባሪ ቡድን ተብሎ መፈረጁን በመቃወም በሶማሊያና በኢትዮጵያ መካካል አሳልፎ የመስጠት ስምምነት እንደሌላቸውም ጠቅሷል።

ለዚህ ድርጊትም የሶማሊያን የደህንነት ኤጀንሲን ጥፋተኛ አድርጓል።

ከኢትዮጵያ መንግሥት ጥያቄን ተከትሎ የሶማሊያ መንግስት አብዲክራም ሼክ ሙሴ በነሐሴ ወር መሰጠቱ የሚታወስ ነው። ይህንም ተከትሎ በሞቃዲሾ የተቃውሞ ሰልፎች ተደርገዋል።

የኮሚሽኑ ሊቀ-መንበር አሊ የሱፍ እንደተናገሩት ” የኦጋዴንን ብሔራዊ ነፃ አውጭ ግንባር አሸባሪ ቡድን ብላ የፈረጀችው ኢትዮጵያ ናት። ሶማሊያ የኢትዮጵያን መንገድ ልትከተል አይገባም” ብለዋል።

የሶማሊያ የፓርላማ አባላት የኮሚሽኑን ሪፖርት በአንድ ድምፅ ያለምንም ተቃውሞ ተቀብለውታል።

በተቃራኒውም የሶማሊያ መንግስት አብዲክራም ከአልሸባብ ጋር ግንኙነት ያለውና ለአካባቢው አደጋ በማለት ድርጊታቸው ትክክል እንደሆነ ይገልፃሉ።

የኢትዮጵያ ባለስልጣናት ለአስተያየት ሊገኙ አልቻሉም።

የኦጋዴን ነፃ አውጭ ግንባር ማንነት

የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጭ ግንባር በአውሮፓውያኑ 1984 ተመሰረተ። ሶማሊኛ የሚናገሩ አርብቶ አደሮች ከማዕከላዊው መንግስት መገለል ይደርስባቸዋል በሚልም ከኢትዮጵያ ነፃነትን ለማግኘት የሚታገል ድርጅት ነው።

የኢትዮጵያ መንግስትም በሶማሌ ክልል እንዲሁም በአዲስአበባ ለብዙ ህይወት መቀጠፍ ምክንያት የሆኑትን የቦምብ ፍንዳታዎችን በማድረስ ድርጅቱን ተጠያቂ ያደርገዋል።

የተወካዮች ምክር ቤትም ድርጅቱን ከስድስት አመት በፊት አሸባሪ በሚልም ፈርጆታል።