December 1, 2017 አጠቃላይ

በመጀመሪያ ህወሐት ነበር። ህወሓትም በደደቢት በበረሃ ይኖር ነበር። ህወሐትም እንዲህ አለ። “በአምሣያችን ኦህዴድን እና ብአዴንን እንፍጠር”! ህወሐትም ኦህዴድን በሻእብያ ከተማረኩ የኢትዮጵያ ወታደሮች እና ብአዴንን ደግሞ ከኢህአፖ የበረሃ ቅሬቶች አበጃቸው።

በአፍንጫቸውም የህወሐትን ማንፌሥቶ እፍ አለባቸው። ህወሐትም እንዲህ አላቸው! “እነሆ የሚቃወሙትን ግደሉ፣ የሚታሠረውንም እሠሩ፣ የሚዘረፈውንም ሁሉ ዝረፋ፣ ተቆርሦ የሚሠጠውንም መሬት ሳትሰስቱ ስጡ፣ በዚያ በነገሳችሁበት ያለውን ሁሉ እንደኔ ሆናቹ ግዙ፣ ሁሉን ታደርጉ ዘንድ ይቻላችኋልና።

እንደቃሉም ሆነ በሺዋች የሚቆጠሩም ሞቱ፣ የቀሩት በየእስርቤቱ እንዲሰቃዩም ሆነ ..መሬትም ንብረትም ተዘረፈ…ህወሐትም ይህን ባየ ግዜ ደስ አለው በልቡም ሀሴትን አደረ

አንድ ነገር ግን ፈጽሞ እንዳታደርጉ አላቸው። ይኸውም ህወሐት ለምን የበላይነቱን ያዘ ብላችሁ እንዳትጠይቁ። ይህን በጠየቃችሁ ጊዜ የሞት ሞትን ትሞታላችሁ አላቸው።

የመጀመሪያዎቹ የኦህዴድ እና የብአዴን ሰዎች ፈጣሪያቸው ህወሐት እንዳላቸው አደረጉ። ለፈጣሪያቸው ታዛዥ ሆኑ፣ የወርቅ፣ የቆዳ፣ የቡና፣ የቅቤ፣ የሠንጋ እና የጤፍ መስዋዕት አቀረቡ። ፈጣሪያቸው ህወሐትም በቀረበለት መስዋዕት ተደሰተ።

እውነት እውነት እላችኋለሁ፣ የሰባውን ጠቦት፣ የደለበውን ሠንጋ፣ ለጋውን ቅቤ፣ ለፈረንጅ ከሚሸጠው ቡና፣ ማኛውን ጤፍ። ከልጆቹ ነጥቆ፤ ለፈጣሪው ህወሐት መስዋዕት ሳያቋርጥ የሚያቀርብ ሁሉ በኔ ዘንድ የተባረከ እና የተቀደሰ ነው አለ።

የመጀመሪያዎቹ የብአዴን እና የኦህዴድ ትውልዶች የፈጣሪያቸውን ትዕዛዝ አንዲትም እንኳን ሣይሸራርፉ እንደተባለው ሲያደርጉ እንሆ 26 አመታት ሆነ።

ህወሐትም ኦህዴድን እና ብአዴንን በመፍጠሩ አንዳች አልተፀፀተም። እነሱም እንዳታደርጉ የተባለውን የስልጣን እና የህይወት ዛፍ አንዲትም ቅርንጫፍ እንኳን አልነኩምና።

አሁን ግን የብአዴን እና የኦህዴድ ልጆችና የልጅ ልጆች አፈነገጡ። የአባቶቻቸውንና የአባቶቻቸው ፈጣሪ የሚሏቸውን ትእዛዝ አንቀበልም ብለው አመፁ፡፡

የደለበውን ሠንጋ፣ ለጋውን ቅቤና ማር፣ የሰባውን ሙክት፣ ማኛውን ጤፍ፣ ውድ የሆነውን ወርቅ፣ የበሰለውን ቡና እና ፈረሱላ ቀይ በርበሬ ለልጆቻችን እናበላለን። ሸጠን ለልጆቻችን መጫሚያና ጥብቆ እንገዛለን ብለው ወሰኑ።

በውሳኒያቸውም ፀኑ። የኢትዮጵያ ህዝብም፣ በውጭም በውስጥም ያለው ተግባራቸውን ደገፋቸው።

ለደቡቦቹም ወንድሞቻቸው ጥሪ አቀረቡ፦ በፈጣሪያቸው በመለሰ ዜናዊ ሣንባ የሚተነፍሱትን ፣ ሽፈራው ሽጉጤን እና ኃይለማርያም ደሳለኝን አስወግደው ፣ ለፈጣሪያቸው ለህወሐት የሚጋዘውን ቡና ፣ ቅቤ ፣ ማር ፣ ወርቅ፣ ቆጮ፣ ቡላ፣ ክትፎ ለራሳቸው ልጆች እንዲያበሉ መከሩ።

የአባቶቻቸውን ፈጣሪ ህወሐትን በነፃ ከሚቀለብ ባለ አስር ጭንቅላት ዘንዶ ጋር አመሳሰሉ።
ለአፋሮቹም፣ ለኦጋዴኖቹም፣ ለጋምቤላዎቹም፣ ለቤኒሻንጉሎቹም ወገኖቻቸው የነሱን ምሳሌ እንዲከተሉ ጥሪ አቀረቡ። ድር ቢያብር አንበሳ እንደሚያስር ለህፃናት ልጆቻቸው አስተማሩ።

ፈጣሪ ህወሐትም ኦህዴድን እና ብአዴንን በራሱ እስትንፋስ ፈጥሯቸዉ ከትእዛዙ በማፈንገጣቸው እጅግ አዘነ፣ ተፀፀተ… ፈራ፥ ደነገጠም፥ ….በልጅ ልጆቻቸው የሚደርስ እርግማን እንደሚያወርድባቸው ነገራቸው…. እንደሚበቀልም አስጠነቀቃቸው።

Source: ethiothinkthank.com/…