13 December 2017

ታምሩ ጽጌ

በትግራይ ክልል በአዲግራት ዩኒቨርሲቲ የተቀሰቀሰ ግጭት ወደ ሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች መዛመቱ ተገለጸ፡፡ በሕይወትና በአካል ላይ ጉዳት ደርሷል፡፡

በአዲግራት ዩኒቨርሲቲ በተማሪዎች መካከል በተነሳ ግጭት አንድ ተማሪ ሲሞት፣ ከ20 በላይ ተማሪዎች ላይ ጉዳት መድረሱን ማረጋገጥ ተችሏል፡፡ በኦሮሚያ ክልል ወለጋ ዩኒቨርሲቲም በተመሳሳይ በተፈጠረ ግጭት ሁለት ተማሪዎች ሕይወታቸው ማለፉን፣ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ አዲሱ አረጋ አስታውቀዋል፡፡

በአዲግራት ዩኒቨርሲቲ በተማሪዎች መካከል ግጭት የተፈጠረው ኅዳር 29 ቀን 2010 .. አመሻሽ ላይ ነው፡፡ ግጭቱ የተቀሰቀሰው ተማሪዎቹ የብሔር ብሔረሰቦችን በዓል በማስመልከት የተለያዩ ዝማሬዎችን በማሰማት ላይ እያሉ መሆኑን፣ የነበረው ሰላማዊ እንቅስቃሴ በደቂቃዎች ውስጥ ወደ ብጥብጥ ተቀይሮ ድንጋይ ውርወራ መጀመሩን ሪፖርተር ያነጋገራቸው ተማሪዎች ተናግረዋል፡፡

የተማሪዎቹ ግጭት የጀመረው ኅዳር 24 ቀን 2010 .. በወልዲያና በመቐለ ከተማ እግር ኳስ ቡድኖች መካከል በወልዲያ ከተማ ሊደረግ የነበረ ግጥሚያን ምክንያት በማድረግ፣ በደጋፊዎች መካከል ከግጥሚው በፊት ተከስቶ የነበረውን ግጭት ተከትሎ መሆኑን ተማሪዎቹ ጠቁመዋል፡፡ በተማሪዎች መካከል ብሔር ተኮር ተቃውሞ በመሰማቱና፣ ከሌላ ክልል የመጡ ተማሪዎች ከግቢ እንዲወጡ የሚገልጽ ተቃውሞ በመነሳቱ ሳቢያ በተፈጠረ ግርግር፣ አንድ ተማሪ መሞቱን የአማራ ክልል መንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ዋና ዳይሬክተር አቶ ንጉሡ ጥላሁን አስታውቀዋል፡፡ ሌሎች ሁለት ተማሪዎች እንደሞቱ የተገለጸ ቢሆንም፣ ሪፖርተር ማተሚያ ቤት እስከገባበት ማክሰኞ ምሽት ድረስ የተረጋገጠ ነገር አልተገኘም፡፡

ማክሰኞ ታኅሳስ 3 ቀን 2010 .. ከቀትር በኋላ ግን በግጭቱ ምክንያት ታስረው የነበሩ በርካታ ተማሪዎች በመፈታታቸው፣ በዩኒቨርሲቲው ፀጥታ መስፈኑንና በተማሪዎች መካከል መረጋጋት መፈጠሩን ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡

የአዲግራት ዩኒቨርሲቲን ግጭት በሚመለከት ማብራሪያ እንዲሰጡ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የትግራይ ክልል ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ገብረ ሚካኤል መለስ፣ የተከሰተው ግጭት መረጋጋቱንና ሰላም እየሰፈነ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

ከዚህ ጋር በተያያዘ በወልዲያ ዩኒቨርሲቲም የተወሰነ ረብሻ የታየ ቢሆንም፣ መረጋጋት መፈጠሩን ለማወቅ ተችሏል፡፡

በወለጋ ዩኒቨርሲቲ በተነሳ ግጭት ሁለት ተማሪዎች መሞታቸው ቢረጋገጥም ማንነታቸው ግን አልተገለጸም፡፡ አቶ አዲሱ እንደገለጹት ግን፣ በተማሪዎቹ ሞት የተጠረጠሩ በርካታ ሰዎች በቁጥጥር ሥር ውለዋል፡፡

በአዲግራት የተቀሰቀሰው የተማሪዎች ተቃውሞ ወደ ጎንደርና አምቦ ዩኒቨርሲቲዎችም መዛመቱ ተጠቁሟል፡፡