ፖለቲካ
ግብፅ የህዳሴ ግድቡን ቦንድ ለመግዛት ጥያቄ አቅርባ እንደነበር ታወቀ

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

13 December 2017

ዘመኑ ተናኘ

ግብፅ የህዳሴ ግድቡን ቦንድ ለመግዛት ጥያቄ አቅርባ እንደነበር ታወቀ

ከስድስት ዓመት በፊት መሠረቱ ተጥሎ በመገንባት ላይ ያለውን የኢትዮጵያ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ቦንድ ለመግዛት፣ የግብፅ መንግሥት ጥያቄ አቅርቦ እንደነበር ታወቀ፡፡

ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ አንድ ከፍተኛ ባለሥልጣን ለሪፖርተር እንዳረጋገጡት፣ ግብፅ የህዳሴ ግድቡን ቦንድ ለመግዛት ጥያቄ ብታቀርብም፣ ኢትዮጵያ ግን ውድቅ አድርጋዋለች፡፡ እንደ ኃላፊው ገለጻ፣ ግብፅ ቦንድ ለመግዛትና የግብፅ ኢንጂነሮች ግንባታውን እንዲያግዙ ጥያቄ ብታቀርብም ውድቅ ሆኖባታል፡፡

ባለፈው ሳምንት የግብፅ ባንኮች የህዳሴ ግድቡን ቦንድ ገዝተዋል የሚል ዘገባ እንደተሠራጨ የሚታወስ ሲሆን፣ የግብፅ ማዕከላዊ ባንክ ገዥ ታሪክ አሚርን ጠቅሶ የግብፅ ‹‹ኢንዲፔንደንት›› ጋዜጣ እንደ ዘገበው የህዳሴ ግድቡን ቦንድ የገዛ የግብፅ ባንክ የለም፡፡

የባንኩ ገዥ ታሪክ አሚር፣ ‹‹ባለፉት ሁለት ቀናት የህዳሴ ግድቡን ቦንድ በ35 በመቶ የወለድ መጠን ገዝተዋል በማለት በማኅበራዊ ሚዲያዎች የተለቀቀው የባንኮች ዝርዝር ውሸት ነው፤›› ብለዋል፡፡

‹‹እየተሠራጨ ያለው መረጃ የባንኮችን ሥራ ለማደናቀፍ የታለመ ነው፤›› ሲሉ የባንኩ ገዥ አስረድተዋል፡፡ ሦስቱ አገሮች በህዳሴ ግድቡ አሞላልና አለቃቀቅ፣ እንዲሁም አካባቢያዊ ተፅዕኖ ለማስጠናት ‹‹ቢአርኤል›› የተሰኘውን የፈረንሣይ ኩባንያ ቀጥረው ለማሠራት ቢስማሙም በመነሻ ሐሳቡ ላይ ስምምነት መድረስ አልቻሉም፡፡

በቅርቡ የግብፅ ፕሬዚዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ፣ ‹‹የናይል ወንዝ ለግብፃውያን የሞትና የሕይወት ጉዳይ ነው›› ማለታቸው የሚታወስ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ በበኩሏ፣ ‹‹ድህነትን ማጥፋት የሞትና የሽረት ጉዳዩ በመሆኑ ድህነታችንን ለማስወገድ ወንዛችንን እንጠቀማለን፤›› ማለቷ አይዘነጋም፡፡

የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የመሠረት ድንጋይ በተጣለ ማግሥት የግብፅ መንግሥት ዓለም አቀፍ አበዳሪ ተቋማትና አገሮች ለግድቡ ዕርዳታ እንዳያደርጉ ግፊት ማድረጉ የሚታወስ ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስተያየት እንዲሰጥ ጥረት ቢደረግም አልተሳካም፡፡

Source    –   Ethiopian Reporter