ታህሳስ 2017

ከመሰረቱ በህዝቦች መካከል ቅራኔ የለም። ሁሉም ሰርቶ በሰላም መኖር ብቻ ስለሚፈልግ ቅራኔ ውስጥ የሚገባበት ምክንያት የለውም።ኣምባገነን ገዢዎች ግን በስልጣን ብሎም በጥቅም ማካበት ዙርያ ስለሚጠመዱ ከህዝቡ ጋር ቀጣይ ቅራኔ ውስጥ ይገባሉ፣ህዝቡ ተባብሮ እንዳይነሳባቸውም ኣንዱን ወገን ከሌላው ጋር እያጋጩ መቆየት ዋናው ስልት ኣድርገው ይጠቀሙበታል።ይኸው ስልታቸው ገፍቶ-ገፍቶ ኣሁን ሃገራችንን የመከፋፈል ጠርዝ ላይ፣ ህዝቦቻችን ደግሞ እርስ በርስ የመጨካከን ስነ-ልቦና ውስጥ እየከተታችው ይገኛል።

ኣብዛኛው (80%) የኢትዮጵያ ህዝብ ኣርሶ-ኣደር መሆኑ ይታወቃል። በብዛት ቀጥሎ ያለው ሰርቶ-ኣደሩ ነው።ኋላ-ቀር ያልሆነው፣ደግ ኣሳቢው ዴሞክራት ደግሞ የነዚሁ ብዙሃን ወገን ነው።ሆኖም እነዚሁ ሰላም ናፋቂያው ዜጎች በጥቂቶቹ መሰሪ ገዢዎች ሴራ ምክንያት ሲተላለቁና ሃገርም የመገነጣጠል ዳመና ሲያንዣብብባት ማየት ህሊና ላለው ፍጡር እጅግ ያሳዝናል።ማዘን ብቻውን ግን መፍትሄ ኣይሆንም።

በሃገራችን እየታየ ያለው የርስ በርስ ግጭት መንሰኤ፣ ስልጣን በጨበጠው የስብሃትነጋ፣ ኣባይ ጸሓየና ስዩም መስፍን ቡድን ትግራይን የመገንጠል ዓላማው ለማሳካት ረዘም ባለ ጊዜ ውስጥ በዘራው መርዛም ቅስቀሳና ኢፍትሃዊ ኣሰራር ላይ የተመሰረተ መሆኑ ማንም ኣርቆ ኣሳቢ ወገን ሊገነዘበው የሚችል ሃቅ ነው። ኣሁንም ገዢዎቹ ይህን ቆማጣ ዓላማቸውን ለማሳካት ሲሉ በሰላዮቻቸው ኣመካይነት ዋልጌዎችን በማሰማራት የመተላለቁ ሂደት እንዲቀጥል እያደረጉ ነው።በዚህ ኣረመንያዊ ተግባር የሚተባበሩ ኣንዳንድ የዋሆች ብቅ ሲሉና ከዚሁ ገዢ ቡድን የማይተናነስ የጥላቻ መርዝ የሚረጩ ፖለቲከኞችና የሚዲያ ሰዎች ሲበራከቱ ደግሞ ሁኔታው የበለጠ ኣስከፊና ውስብስብ ያደርገዋል።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ብሄር ተኮር ግጭቶችና ግድያዎች እየተበራከቱ ነው፣ የተለያዩ ሚድያዎችና ጋዜጠኞችም በተለያየ መልክ ይዘግቧቸዋል።ሰሞኑን “በትግራይ ኣዲግራት ዩኒቨርሲቲ የኦሮሞና የኣማራ ተማሪዎች ዩኒቨርሲቲውን ለቀው እየወጡ ነው” በሚል ርእስበ 10/12/2017 ዘ-ሃበሻድረ-ገጽ የጋዜጠኛ ሙሉቀን ተስፋው ሪፖርት ዋቢ በማድረግ እንደሚቀጥለው ዘግበዋል። “. . . ሶሰት ያክል ተማሪዎች ተገድለዋል በመቶዎች የሚቆጠሩ ኣካላዊ ጉዳት ደርሶባቸዋል” ይልና ወረድ ብሎ የመፍትሄ ሓሳብ በሚል“. . . ሌላው ግን ሁላችንም ለመበቀል የግድ ትግራይ ድረስ መሄድ ያለብን ኣይመስለኝም። በኣካባቢህ ያሉ ወያኔዎችን በማንኛውም መልኩ መታገል ነው።ያኔ ማን የበለጠ እንደሚጎዳ እናያለን” ይላል።በየኣከባቢው ከጥንቱ ጀምሮ ሰርቶ-ኣደር የትግራይ ህዝብ ለስራ እንደተሰማራ እየታወቀ፣ ‘’ወያኔዎች’’ በሚል ሽፋን ህዝቡ ላይ የበቀል ጥቃት ለመፈጸም መቀስቀስ፣ገዢውና ተገዢው ህዝብ፣ ጨቋኝና ተጨቋኙ ወገን የማይለይ፣ጸረ-ህዝብ ውጥን ነው። በተመሳሳይ መንገድ፣የጎንደር ሕብረት ለኢትዮጵያ ኣንድነት በ12/12/2017 ‘‘በመቀሌና ኣዲግራት በትግርኛ ተናጋሪ ያልሆኑ ተማሪዎች የደረሰው ግድያና ድብደባ በመቃወም’’ ባስተላለፈው ጥሪ “. . . ሓዘናችን ለትግራይ ህዝብ የወደፊት እጥፈንታም ጭምር እንጂ” ይልና ቀጥሎም “ . . . በክልሉ ውስጥ እየተፈጸመ ላለው ኣረመኒያዊ ወንጀል ምንም ዓይነት ተቃውሞ ኣለማሰማቱ ለሚመጣው ኣጸፋ እራሱን እያጋለጠ፣ . . .”በማለት መፈናፈኛ ባጣው ጭቁን የትግራይ ህዝብ ላይ ዛቻውን ያስተጋባል።ይህን የመሰለ ኣጥፊ ቅስቀሳ ኣምና በኢሳት ቴለቪዥን ተለቆ ማዳመጣችን ይታወሳል።

በውነቱ ይህ ጥሪ ሃገራችን ለገባችበት ኣሳዛኝና ኣደገኛ ቀውስ የመፍትሄ ሓሳብ ጠቋሚ ሳይሆን ችግሩን የሚያባብስና ቀጣይ የርስ በርስ እልቂት የሚጋብዝ፣ ሓላፊነት የጎደለው ቅስቀሳ ነው። የገዢው ቡድን ጨለምተኛ ዓላማን እንዲሳካ የሚያግዝ ግልብ ስሜታዊነት ነው። “የበለጠ የሚጎዳ እናያለን” እያሉ፣የትም ይሁን የት ህዝብ ሲጎዳ ለማየት ከመቀስቀስና ከመጠበቅ ይልቅ ማንም የሰው ልጅ እንዳይጎዳ መታገል ታላቅነት ያስብል ነበር።ስሕተትን በስሕተት፣ ወንጀልን በወንጀል፣ ጥፋትን በሌላ ጥፋት ለመመለስ መጣር የመፍትሄ ሓሳብ ሳይሆን ተያይዞና ኣብሮ የማለቅ፣ በጥላቻ የሰከሩ የግብዞች ስራ ነው። ይህ ውጥን ጤነኛ ኣእምሮ ካለው የሰው ፍጡር የሚጠበቅ መፍትሄ ካለመሆኑ ባሻገር በዓለም-ኣቀፍ ህግ የሚያስጠይቅ ወንጀልም ነውና፣ ይልቅ ስለገንቢ መፍትሄ ብንረባረብና ለዚህ ያደረሰን ገዢ-መደብ ነጥለን በመምታት ሁላችንም ተጠቃሚዎች የምንሆንበት ለህግ የሚገዛ በሳል ኣመራር እንዲፈጠር መታገልና መጣር ይሻላል እንላለን።

ኣሁን በቅርብ ጊዜ በኣማራውና በኦሮሞው መካከል የተጀመረው የህዝቦች መቀራረብ ገንቢና ኣምባገነኖቹ የጠነጠኑት የመከፋፈል ሴራን ባዶ የሚያስቀር መሆኑ ታውቆ፣ ይህ በጎ ጅምር በሁለቱ ህዝቦች ብቻ ሳይወሰን ሌሎቹ ህዝቦችም በማካተት ሃገር-ኣቀፍ ተሳትፎ እንዲኖረውና ገዢው ቡድን እርቃኑን በማስቀረት የጋራ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት መስርተን በሰላምና በእኩልነት ለመኖር መመኘት ብሎም መታገል እንጂ “ማን የበለጠ እንደሚጎዳ እናያለን”፣“ለሚመጣው ኣጸፋ እራሱን እያጋለጠ”፣ እያሉ ለጥፋት መነሳሳት ህዝባዊ ወገንነትንና የኢትዮጵያ ኣንድነትን መገዝገዝ መሆኑ ከወዲሁ ሊገባን ይገባል።

ያንድን ኣካባቢ ህዝብ ነጥሎ የመምታት ኣባዜ ቀደም ሲል በኣማራውና በኣኝዋኩ፣ በኦሮሞውና በደቡብ ኦሞው፣ ቀጥሎ በትግራዩና ጨለንቆው፣እንደዚሁም በሌሎች ኢትዮጵያውያን ወገኖች በተከታታይ እየታየ ነው። ይህ ኣውዳሚ – በብሄር ላይ ያተኮረ የርስ በርስ ግጭት ህወሓት/ኢህኣዴግ ስልጣን ላይ ከወጣ ወዲህ የመጣ እንጂ በሃገራችን ኣልነበረም። ስለሆነም ስር እንዳይሰድና ከቁጥጥር ውጭ ሄዶ፣ ተመልሶ እኛንኑ ብሎም ሃገራችንን ሳያወድም ተባብረን ልንገታው ያስፈልጋል። የትግራይ ህዝብም በስሙ እየነገዱ ያወረዱበትን ግፍና ጭቆና ተቋቁሞ፣ በሌላው ኢትዮጵያዊ ወገኑ እየደረሰ ያለውን ግድያም ይሁን ወከባ ኣጥብቆ መቃወም ይጠበቅበታል።ይህ እንዲሆን የሁላችን ትብብር እጅግ ኣስፈላጊ ነው።በዚህ ገንቢ ፈለግ ትግላችንን ካስተካከልንና የእያንዳንዳችን ኣስተዋጽኦ ከታከለበት ውጤቱ ያማረ፣ሁላችን ተጠቃሚ የሚያደርግ፣ እንደዚሁም ከፍተኛ ቀውስ ውስጥ ገብታ ያለችው ታሪካዊት ሃገራችን ለማዳን እንችላለን። ገንቢ መፍትሄ ማለት ይህነኑ በመሆኑ በዚሁ ፈለግ ላይ እንረባረብ።

የተባበረ ህዝብ የገዢዎቹ ሴራ ያከሽፋል!!!

ኢትዮጵያውያን ተጋሩ የውይይት መድረክ