አራቱ የኢህአዴግ አባል ድርጅት መሪዎች ባለፈው ሳምንት የተጠናቀቀውን የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ስብስባ ውሳኔን በተመለከተ መግለጫ ሰጥተዋል።

ይህን ተከትሎም ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በእስር ላይ የሚገኙ ፖለቲከኞችና ሌሎች ግለሰቦች ክሳቸው ተቋርጦ ወይም በምህረት እንዲፈቱ መወሰኑን ተናግረዋል። ከሰዓታት በኋላ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽህፈት ቤት የፌስ ቡክ ገፅ ላይ ከላይ የሰፈረው ጽሁፍ ተሻሽሎ በራሳቸው የጥፋት ድርጊት ምክንያት በአቃቢ ህግ ጉዳያቸው ተይዞ በእስር የሚገኙና የተፈረደባቸው የተለያዩ ፖለቲከኞችም ሆነ ሌሎች ግለሰቦች የተሻለ ሃገራዊ መግባባት ለመፍጠርና የዲሞክራሲ ምህዳሩን ለማስፋት በማሰብ ክሳቸው ተቋርጦ ወይም በምህረት ህግና ህገመንግሥቱ በሚፈቅደው መልኩ እንዲፈቱ ተወስኗልበሚል ቀርቧል። የኢትዮጵያ መንግሥት የፖለቲካ እስረኞች ይፈታሉ መባሉን አስተባብሎ የተወሰኑ የፖለቲካ ፓርቲ አባላት ብቻ ምህረት ወይም ክሳቸው ተቋርጦ እንደሚለቀቁ ገልጿል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ ረዳት እንዳሉት የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት ሲባል ሁሉም የፖለቲካ እስረኞች ይፈታሉ የሚለው በስህተት የተጠቀሰ ነው ሲል መንግሥት ለመገናኛ ብዙሃን ገልጿል። ይህን ተከትሎም በማህበራዊ ሚዲያ ላይ እነማን ሊፈቱ ይችላሉ በሚለው ላይ ብዙዎች የተለያየ አስተያየት ሰጥተዋል።

በተለይ የፖለቲካ እስረኞች እነማን ናቸው?’ የሚለው ጉዳይ የብዙዎች ርዕሰ ጉዳይ ነበር። በማንኛውም ፖለቲካዊ በሆኑ ጉዳዮች መንግሥት አንድን ግለሰብ ከፖለቲካ ምህዳር ውጭ ለማድረግ በማሰብ ከከሰው፣ ካሰረው እንዲሁም ከተፈረደበት የፖለቲካ እስረኛ ይባላልይላሉ በኪል ዩኒቨርሲቲ የሕግ መምህር የሆኑት ዶ/ር አወል ቃሲም አሎ። ሆኖም የፖለቲካ እስረኛ ለሚለው ቃል የሚሰጠው ትርጓሜ ብዙ ነው የሚሉት ዶ/ር አወል ወንጀል ፈጽመው የታሰሩ ሰዎችም እንደፖለቲካ እስረኛ ሊቆጠሩ ይችላሉ ይላሉ። ወንጀል ፈጽመው ሊሆን ይችላል። ነገር ግን ወንጀሉን መፈጸም አለመፈጸማቸው ሳይሆን ዋናው ጉዳይ፤ የተከሰሱትና የተፈረደባቸው ፖለቲካዊ ጉዳይ ስላለ እንጂ የፖለቲካ ግጭት ባይኖር ወንጀሉን ፈጽመውም ላይታሰሩ ይችላሉ። ስለዚህ ከመያዛቸው፣ ከመታሰራቸው እና ከፍርዳቸው ጋር ተያይዞ ዋነኛው ትርጓሜ የፖለቲካ መነሻ መኖሩ ነውሲሉ ይገልጻሉ። ይህ አገላለጽ ግን በሁሉም በኩል ተቀባይነት የለውም።  የፖለቲካ እስረኛ አከራካሪ ቃል ነው የሚሉት የአምንስቲ አንተርናሽናል የአፍሪካ ቀንድ የሰብዓዊ መብቶች ጉዳይ አጥኚ የሆኑት አቶ ፍሰሃ ተክሌ ተቋሙ የፖለቲካ እስረኛ የሚለውን ቃል መጠቀም አይፈልግምይላሉ።

የፖለቲካ እስረኛ ብዙ ነገር ያጠቃልላል። እንደመፈንቅለ መንግሥት ያሉ ወንጀሎችን የፈጸሙም እንደፖለቲካ እስረኛ ሊቆጠሩ ይችላሉ። በሃይል ወይንም በተመሳሳይ መንግሥትን ለመገልበጥ ባደረጉት ሙከራ ቢታሰሩ የፖለቲካ እስረኞች ናቸው ግን ወንጀል ፈጽመዋል። ስለዚህ ይህን መሰሉን ውዥንበር ለመቀነስ የፖለቲካ እስረኛ ከማለት ይልቅ የህሊና እስረኛ የሚለውን እንጠቀማለንይላሉ። የህሊና እስረኛ የሚለው ሰዎቹ በአቋማቸው ወይንም በፖለቲካ አመለካከታቸው ምክንያት መታሰራቸውን ነው የሚያመለክተው። አምንስቲ አንተርናሽናል ህሊና እስረኛ ለማለት የተለጠፈበትን ወንጀል ሳይሆን መነሻውን ነው የሚያየው የሚሉት አቶ ፍሰሃ አንደኛው መለኪያችን የሚሆነው አንድ ሰው ይህንን በእውነት ፈጽሞታል ወይስ ግለሰቡን\ቧን ባለው የመንግሥት ተቋም ከደርጊቱ/ቷ ለማግለል የተለጠፈ ወንጀል ነው የሚለውን ማየት ያስፈልጋል። መነሻው ማረጋገጥ ቀላል አይደለም ግን በቀላሉ የምንረዳው ነገር ነው። ፈጽመውታል የተባለው ወንጀልስ ትክክለኛ ነው ወይ? በተጨማሪም ተጣሰ የተባለው ጉዳይስ የዓለም አቀፍ ህጎችን ያሟላ ነው የሚለው ይታያልብለዋል። የመድረክ ምክትል ሊቀምንበር እና የውጭ ጉዳይ ኃላፊ ዶ/ር በየነ ጴጥሮስ በበኩላቸው በቀጥታ በፖለቲካ ተሳትፎው በይፋ ህዝብ የሚያውቀው፤ በኢትዮጵያ የፖለቲካ አዋጅ መሠረትም የፖለቲካ ፓርቲ አቋቁመው የሚመሩ፤ መሪዎቹ በመጀመሪያው ረድፍ ይቀመጣሉ። ከዚያ በኋላ ደግሞ እነርሱ ስር የሚንቀሳቀሱ የበታች አባሎች፣ አመራሮቻቸው እንደዚሁ የፖለቲካ እስረኛ ይባላሉይላሉ። በተዘዋዋሪ ደግሞ ለፖለቲካ ፓርቲዎች በገንዘብም ሆነ በሃሳብም እንዲሁም በሌላ መንገድ ድጋፍ ሰጥታችኋል በሚል የሚታሰሩ ዜጎች ደግሞ አሉ የሚሉት ዶ/ር በየነ በውጭ ሃገር የሚንቀሳቀሱ ሥርዓቱ ነውጠኞች ብሎ ከፈረጃቸው ጋር ግንኙነት ነበራችሁ ተብለው የሚታሰሩትም የፖለቲካ እስረኞች ይባላሉብለዋል። ለዶ/ር አወል የፖለቲካ እስረኞች እነማናቸው የሚለውን የሚወስነው መንግሥት ነው። አሳሪም ፈቺም እሱ ስለሆነ እዚያ ምደባ ውስጥ የሚወድቁትን ራሳቸው ናቸው የሚወስኑትይላሉ።

የመንግሥት መግለጫን ተከትሎም በርካቶችን እያነጋገረ ያለው ጉዳይም እንማን እንደሚፈቱ አለመታወቁ ነው። ስለዚህ መንግሥት በሚሰጠው ውሳኔ መሰረት የሚፈቱና በእስር ቤት የሚቆዩ ሊኖሩ ይችላሉ።

BBC