ለኦህዴድ ቅርበት ካላቸው ጦማሪዎች መካከል አንዱ ደረጄ ገረፉ ቱሉ ነው። የሚጽፋቸው ጽሁፎች ይመቹኛል። ከዚህም የተነሳ በመደበኛነት የምከታተለው ጦማሪ ነው። የአቶ ሃይለማሪያምን መልቀቅ ተከትሎ ጠቅላይ ሚኒስተር ከኦህዴድ መሆን እንዳለበት ይከራከራል። “አንድ ነገር በጣም ግልፅ ነው። ቦታውን እንፈልገዋለን። ምክንያቱ ደግሞ አሁን ሀገሪቷንም ሆነ ኢህአዲግ የገጠመውን ችግር መፍታት የሚችል ብቃት ያለው፣በመላው ህዝብ ተቀባይነት ያለው እና በማንኛውም መልኩ legitimate የሆነ ሰው ማቅረብ የምንችለው እኛ ስለሆንን” ይላል ደሬጄ። ይመስለኛል እነ አቶ ለማ መገርሳን አስቦ ነው።
 
ሌላው የኦሮሞ አክቲቪስት ጃዋር መሐመድ ደግሞ ከሚኔሶታ፣ ማን ጠቅላይ ሚኒስተር መሆን እንዳለበት ሲጽፍ ” Appoint Lemma Megersa፣ Chairman of EPRDF and ( acting) PM immediately ” ይላል። ብዙ ጊዜ ከጃዋር ጋር አልስማም፤ ግን አሁን መስማማት ይኖርብኛል። ለአቶ ለማ መገርሳ ጠቅላይ ሚኒስቴርነት የኔም ልብ ክፍት ነው። ምን አልባት ጃዋር ለማን የደገፈው ኦሮሞነትን መለኪያ በማድረግ ይሆናል። ወገንተኛ በመሆን። እኔ ግን አቶ ለማ ጠቅላይ ሚኒስተር መሆናቸው ላይ ችግር የሌለብኝ፣ ቄሮ ያምጻል ከሚል፣ ወይንም ኦሮሞ ስለሆኑና የዘር መለኪያ በማስቀመጥ አይደለም። ወገንተኛ ብሆን የሸገርን ልጅ ፈልጌ ነበር እርሱ ይሁን የምለው። ግርማ ሰይፉን !!!! ፡) ነገር ግን በትክክል ኦሮሞነትን ትተን በብቃት ኢሕአዴግ ውስጥ ያሉትን ብንመዝን ከለማ የሚሻል ሰው ያለ አይመስለኝም። ካለ ለመስማት ዝግጁ ነኝ። (እርግጥ ነው አቶ ገዱ አንዳርጋቸው አለ ሌላ ብቃት ያለው ሰው። በአሁኑ ወቅት ግን ከነ በረከት ስምኦን ጋር አንገት ለአንገት ተያይዞ እየተፋለመ ነው ያለው)።
 
ለማ መገርሳ እነ አባ ዱላ ገመዳ ያበሰበሱትን፣ ዘረኛ ድርጅትን በመቀየር ወደ አዲስ ምእራፍ ያሸጋገረ፣ ኢትዮጵያዊነትን በማቀንቀን የኢትዮጵያዊነት አዝማች የሆነ ሰው ነው። ያ ብቻ አይደለም ለህዝብ የሚጠነቀቅም ነው። አጋዚ ገብቶ ወጣቶችን እንዳይጨርስ፣ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ብዙ ጊዜ እንዳይታወጅ አድርጓል። አሁን የታወጀዉንም ከነ አቶ ገዱ ጋር በመሆን እንደተቃወሙት ተዘግቧል።፣ አባ ገዳዎችን ይዞ ቄሮዎችን በማግባባት ነገሮችን ለማረጋጋት የሞከረ ሰው ነው። የቻለውን በቅንነትና በትህትና አድርጓል። ከዚህም የተነሳ በአሁኑ ወቅት በኢሕአዴግ ውስጥ ፣ በሕዝብና በተቃዋሚዎች ተቀባይነት ሊኖረው የሚችል ሰው ቢኖር አቶ ለማ ነው ብዬ አስባለሁ።
 
እርግጥ ነው ለማ መገርሳ የፓርላማ አባል አይደለም። በሕግ መንግስቱ አንቀጽ 73 መሰረት ጠቅላይ ሚኒስተር የሚመረጠው ከፓርላማ አባላት ነው። ስለዚህ አቶ ለማ ጠቅላይ ሚኒስተር እንዳይሆን ሕጉ ይከለክለዋል ሊባል ይችላል። ለዚህም መፍትሄው ቀላል ነው። ጃዋር አንድ የጠቀሰው ነገር አለ። “acting” የሚል ቃል። በኔ እይታ ተጠባባቂ ጠቅላይ ሚኒስተር ለመሆን የፓርላማ አባል መሆን የግድ አስፈላጊ ላይሆን ይችላል። ልክ በትግራይ ክልል እንደተደረገው በፌዴራል ደረጃም ማድረግ ይቻላል። ዶር ደብረጽዮን የትግራይ ክልል ምክር ቤት አባል ስላልሆነ የክልሉ አስተዳዳሪ መሆን ስለማይችል፣ ምክትል አስተዳዳሪ ሆኖ ነው እየሰራ እንዳለው።
 
ሁለት ነገሮችን ላንሳና ላቁም።
 
አንደኛ – ክልሉ ሰፊ እንደመሆኑ ሁሉንም ችግሮች አቶ ለማ መፍታት አልቻለም። በተለይም በኦሮሚያ ያሉ የሌሎች ማህበረሰባትን መብቶች በማስከበር ዙሪያ፣ ደፍሮ በኦህዴድ ውስጥ ያሉ የኦነግ ርዝራዦችን ተቋቁሞ ለዉጦችን ማምጣት ተስኖታል። አሁንም ሌሎች በኦሮሚያ ውስጥ ከኦሮሞው በታች ነው የሚቆጠሩት። ትልቅ የዘር መድልዎ አለ። አሁንም ሌሎች ማህበረሰባት በአማርኛ አገልግሎት ማግኘት፣ በክልሉ ሆን በዞንና ወረዳ ቀበሌዎች ተመርጠው ሆነ ተቀጥሮ መስራት አይችሉም። አሁንም ኦሮሚያ የኦሮሞዎች ብቻ ናት። አሁንም በተለያዩ የኦሮሚያ አካባቢዎች ሌሎች ማሀረሰባት ላይ በዘራቸው ምክንያት ጥቃት ይፈጸምባቸዋል። ሌልች በኦሮሚያ ውስጥ ሁለተኛ ዜጎች ናቸው። አቶ ለማ ያንን ማስተካከል አልቻለም።
 
ሆኖም ግን ለማስተካከል ካለመፈለግ የተነሳ ሳይሆን በብዙ ነገሮች ከመወጠሩ የተነሳ እንደሆነ ቅርበት ካላቸው ሰዎች ተረድቻለሁ። እና ምን ማለት ፈልጌ ነው አቶ ለማ ጠቅላይ ሚኒስተር ይሁን ስል ከኢሕአደእግ ውስጥ ተሻለ ስለሆነ እንጂ ፣ በርሱ ላይ ቅሬታዎች ስለሌሉኝ አይደለም ማለቴ ነው። ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ቢደረግ፣ እነ አንዱዋለም አራጌ፣ እነ በላይ በፍቃዱ…እያሉ በምንም ተአምር ለማ መገርሳን ልመርጥ አልችልም።
 
ሁለተኛ – አቶ ለማ ጠቅላይ ሚኒስተር ከሆኑ የአገር ችግር ይፈታል ማለት አይደለም። ሃይለማሪያም እንደሆነው አቶ ለማም በሕወሃት ደህንነቶች ከታጠረና ከተከበበ በቀላሉ ጥቅም የለሽ ሊሆን ይችላል። ትልቁ ነገር ማን ነው ጠቅላይ ሚኒስተሩን የሚይዘው ሳይሆን ጠቅላይ ሚኒስተሩን የያዘው ሰው ምንድን ነው የሚያደርገው የሚለው ነው። ሕወሃትን ያገለግላል ወይስ ህዝብን ያገለግላል ? የኔ ጥያቄ ማን ስልጣን ላይ ይቀመጥ የሚለው አይደለም ? “የኔ ጥያቄዎች የሚከተሉት ናቸው፡
 
1) ዘሬ ሳይጠየቅ ከሁሉም እኩል ሆኜ በሁሉም የአገሪቷ ግዛቶች ሳልሸማቀቅ፣ ሳልፈራ፣ በነጻነት የመኖር ዋስታን አለኝ ወይ ? በአሁኗ ኢትዮጵያ ከአዲስ አበባ ውጭ ደረቴን ነፍቼ መኖር አልችልም። ለምን ከአዲስ አበባ ዉጭ ያሉ ግዛቶች በሙሉ በዘር ተሸንሽነዋል። እኔ ደግሞ ዘሬ ኢትዮያዊነት ነው። ለምሳሌ ከላይም በትንሹ ለማንሳት እንደሞከርኩት በኦሮሚያ የስራ ቋንቋ አፋን ኦሮሞ ብቻ ነው። ኦሮሚያም የኦሮሞዎች ብቻ ናት። አሁን ባለው የክልሉ ሕግ መንግስት መሰረት። በመሆኑም በአዳማ ሸገር ከተወለድኩት ከኔ ይልቅ ሃረርጌና አሩሲ ድንበር የተወለደው ጃዋር የበለጠ መብት አለው። ለምን እርሱ መጀመሮያ ኦሮሞ ስለሆነ እኔ ደግሞ መጀመሪያም መጨረሻም ኢትዮጵያዊ ስለሆንኩኝ። አዳማ የተወለደ ጉራጌ አገርህ አይደለም እየተባለ፣ ጉርሱም የተወለደ ፣ አዋሽን ተሻግሮ የማያውቅ አዳማን የራሱ መሬቱ አድርጎ ይቆጥራል። ኦሮሞ ስለሆነ ብቻ። ብድር ፣ መንግስታዊ ድጋፍ ካስፈለገ ከጉርሱም የመጣው እንጂ አዳማ የተወለደው ከክልሉ መንግስት አያገኝም። ለምን የሁሉም ነገር መለኪያው በኦሮሚያ ውስጥ ኦሮሞነት ስለሆነ።
 
2) ግፍ ሲፈጸምብኝ አቤት የምልበት ፍርድ ቤት አለ ወይ ?
 
3) እኔን የሚያሸብረኝ፣ በዉሸት ክስ የሚያስረኝ፣ ቶርቸር የሚያደርገኝ ሳይሆን እኔን የሚጠበቀኝ የፖሊስና የደህንነት ተቋማት አሉ ወይ ?
 
4) ፕሮፖጋንዳ የሚረጭ ሳይሆን በትክክል ለሕዝብ መርጃ የሚያቀርብ ሜዲያ አለ ወይ ?