Eritrea Orthodox Tewahido faithfuls sunday school2

  • “ከሃይማኖት ላለመናወጥና በሥነ ምግባር ለመጽናት በቤተ ክርስቲያን መሰባሰብ ብቸኛው መንገድ ነው፤”
  • ማኅበሩን በተሐድሶ ኑፋቄ ለመበከል በከፍተኛ ደረጃ ሲንቀሳቀሱ የተጋለጡ ሐሰተኛ ወንድሞች ጉዳይ ለሚመለከተው አካል ተመርቷል፤” /የማኅበሩ ሊቀ መንበር/

†††

(ኢኦተቤ ቴቪ፣ መ/ር መዝገቡ ጌታቸው)

Eritrean Orthodox fathfuls in addis

በኢትዮጵያ የሚገኙ ትውልደ ኤርትራውያን ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን፣ የሰንበት ት/ቤታቸውን አምስተኛ ዓመት ምሥረታ በዓል በአዲስ አበባ ደብረ ፍሥሓ መካነ ሰማዕት ቅዱስ ቂርቆስ ቤተ ክርስቲያን በድምቀት አከበሩ፡፡

የሰንበት ት/ቤታቸውን የምሥረታ በዓል ባከበሩበት ወቅት የአንዲት ምእመንት የጋብቻ ሥነ ሥርዐት ለሰንበት ት/ቤታቸው ምሥረታ ምክንያት እንደኾነ ተገልጿል፡፡

በ2004 ዓ.ም. መስከረም ወር በሥርዐተ ተክሊል በሥጋ ወደሙ የተከናወነውን ጋብቻ ለመከብከብ (ለማጀብ) የተገናኙና በኤርትራ የተለያዩ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ያገለግሉ የነበሩ የተወሰኑ ወንድሞች፣ እኅቶችና አባቶች ከሥነ ሥርዐቱ በኋላ፣ ለምን ተበታትነን እንቀራለን፤ ብለው በመሰባሰብ የሰንበት ት/ቤቱን መሥርተዋል፡፡

በሒደትም ሰውን በሚሰማው ቋንቋ ማስተማር እንደሚገባ ቅዱስ ጳውሎስ የተናገረውን መሠረት በማድረግ በተለያዩ አጋጣሚዎች በመዲናዋ ለሚኖሩ ምእመናን፣ በሚሰሙት ቋንቋ ለምን አናስተምርም በሚል ዓላማ የሰንበት ት/ቤቱ አገልግሎቱን እያጠናከረ መምጣቱ ታውቋል፡፡

የስብከተ ወንጌል መርሐ ግብሩ በደብሩ ዘወትር በየሳምንቱ ቅዳሜ ከቀኑ 8 እስከ 10 ሰዓት እየተካሔደ እንዳለ ተጠቁሟል፡፡

የማኅበሩ አመራሮች ለመርሐ ግብራቸው መቃናት እገዛ ያደረጉላቸውን የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት፣ የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽንና የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት እና የመካነ ሰማዕት ቅዱስ ቂርቆስ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር አመስግነዋል፡፡

Mmr Seare Tekeste

የሰንበት ት/ቤቱ አባላት፣ ከኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ሃይማኖታቸው ላለመናወጥና በሥነ ምግባር ጸንቶ ለመኖር በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር መሰባሰባቸው ብቸኛ መንገድ እንደኾነ በዕለቱ በተላለፈው የሊቀ መንበሩ መ/ር ሰዓረ ተከሥተ መልእክት ተጠቅሷል፡፡

Eritrean Orthodox fathfuls in addis2

በዚሁ የማኅበረ ምእመናኑ አምስተኛ ዓመት የሰንበት ት/ቤት ምሥረታ በዓል አከባበር፥ መንፈሳዊ ዝማሬ፣ የስደትን አስከፊነት የሚያስረዳ ተውኔት እና ትምህርተ ወንጌል ቀርቧል፡፡

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጋራ በዶግማ፣ ቀኖና፣ ታሪክና ትውፊት ምንም ልዩነት የሌላቸውን መንፈሳዊ ልጆቿን ሰብስባ በልማት ኮሚሽን በኩል እገዛ ማድረጓ፣ የሐዋርያዊ ተልእኮዋ አካል በመኾኑ አጠናክራ እንደምትቀጥልበት ተመልክቷል፡፡

Eritrean Orthodox Faithfuls3

ስለ ጉዳዩ አስተያየታቸውን የሰጡት የደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ ፀሐይ በቀለ ተሰማ፣ “የኤርትራ ተወላጅ ወንድሞቻችንና እኅቶቻችን፥ ሃይማኖታቸውን እንዲያውቁ፣ ሀገራቸውን እንዲወዱ ይልቁንም ኹላችንም አንደበታችን ይናገር እንጅ ልባችን እንደሚያምነው ኤርትራ ሀገራችን ናት፡፡ ቀደም ሲልም አንድ ብፁዕ አባት እንደተናገሩትና ልባችን ውስጥ ተቀርጾ እንደቆየው፣ ‘ኤርትራ ራስ ናት’ እንዳሉት እኛም ያን እናምናለን፤ ክርስትናም ድንበር ተሻጋሪ እንደመኾኑ መጠን ከኤርትራ ምእመናን ጋራ በክርስቶስ አንድ እስከኾን ድረስ ቃሉን ማስተማር፣ ለእግዚአብሔር መንግሥት ማዘጋጀት እንደሚገባን እነዚህ ወገኖቻችን በዚህ ደብር ተሰባስበው እንዲማማሩ እያደረግን ነው፡፡ ይህም ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰላምን የምትሰብክ የፍቅር እናት፣ ኹሉንም ሰብስባ የምትይዝ መኾኗን የሚገልጽ በጎ ሥራ ስለኾነ አጠናክረን እንቀጥልበታለን፤” ሲሉ ድጋፋቸውን አረጋግጠዋል፡፡

በሌላ በኩል፣ ማኅበሩን በፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ ለመበከል ከ2008 ዓ.ም. ጀምሮ በከፍተኛ ደረጃ ሲንቀሳቀሱ የተጋለጡ “ሐሰተኛ ወንድሞች” ጉዳይ ለሚመለከተው አካል መመራቱን፣ ሊቀ መንበሩ መ/ር ሰዓረ ተከሥተ ለኢኦተቤ ቴቪ ተናግረዋል፡፡

እንደ አሰግድ ሣህሉ ካሉት ውጉዛን ጋራ ጥብቅ ግንኙነት የነበራቸው እኒህ ሰርጎ ገቦች፡- በነገረ ክርስቶስ፣ ነገረ ማርያም እና ክብረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ እየቀሠጡ ኑፋቄን በጉባኤው ለማስፋፋት ያደረጉት ሙከራ መጋለጡን የገለጹት ሊቀ መንበሩ፣ ማስረጃው ለሊቃውንት ጉባኤ ቀርቦ ውሳኔው እየተጠበቀ እንዳለ አስታውቀዋል፡፡