May 11, 2019

Source: https://ethiothinkthank.com

በያሬድ ሃይለማሪያም

ጠቅላይ ሚንስትር አብይ በተደጋጋሚ አስተዳደራቸው የሕግ የበላይነትን ማስፈን እንደተሳነው ለሚቀርብላቸው ጥያቄ የሚሰጡት ምላሽ እጅግ ግራ የሚያጋባ እና መሰረታዊ የአስተሳሰብ ስህተትም ያለበት ነው። በመጀመሪያ ሕግ ማስከበርን እና ትዕግስትን ምን አገናኛቸው? ተደጋግሞ ለሚቀርብላቸው ጥያቄ ምላሻቸው እንታገስ ብለን ነው፣ ጉልበት አጥተን አይደለም፣ መሳሪያ በእጁ ያለን መንግስት እንዴት ኃይል ተጠቀም ይባላል የሚሉ እና ትላንት በጽ/ቤታቸው አዲስ ወግ በሚል በተዘጋጀው የውይይት መድረክም ላይ አጠንክረው ይሄንኑ አቋማቸውን እንዲህ ሲሉ ገልጸዋል፤ “ከማንም በላይ መንግስት ትዕግስተኛ መሆን አለበት”።ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ሕግ ማስከበር እና የሕግ የበላይነትን ማረጋገጥ ከትዕግስተኝነት ጋር ምን አገናኘው? የትዕግስትዎትስ መለኪያ ምንድን ነው? ሥርዓት አልበኝነቱ ምን ደረጃ ላይ ሲደርስ ነው የእርሶዎ ትዕግስተኝነት የሚያልቀው እና ሕግ ማስከበር የሚጀምሩት? ይህ መንግስት ሕግ በማስከበር በኩል ያሳየው ዳተኝነት ከሳምንት በፊት በተወካዮች ምክርቤት ቀርቦ በአገሪቱ እየታየ ያለው መፈናቀል፣ ግድያና ዝርፊያ እንዲሁም የመሳሪያ ዝውውር እና ሌሎች የወንጀል አድራጎቶች መበራከት ዋነኛው ምክንያት አስፈጻሚው አካል የተጣለበትን ሕግ የማስከበር እና ሥርዓት የማስፈን ኃላፊነቱን በአግባቡ ስላልተወጣ መሆኑ ጠንከር ባለ ቋንቋ ተገልጾ ፓርላማው ለአስተዳደርዎም ጥብቅ ማሳሰቢያ መስጠቱን ሰምተን ለፓርላማው ወፌ ቆመች ብለናል።

እንደ እኔ እምነት ከሕግ የበላይነት ጋር በተያያዘ ይህ አይነቱ የተዛባ አስተሳሰብ በእርሶ ደረጃ ካለ ሰው ሊመነጭ የሚችለው በሁለት ምክንያቶች ይመስለኛል፤

በዚሁ መድረክ ላይ መንግስት እርምጃ መውሰድ በፈለገ ጊዜ የሚሳነው ነገር እንደሌለ ገልጸው ጭራሽ ስላቅ በሚመስል አኳኋን አገሪቱ የሕግ የበላይነትን በማስከበር እረገድ የገጠማት ችግር በሚመከርበት መድረክ እርሶ መንገድ እናጽዳ የሚል የመፍትሔ ሃሳብ ማቅረብዎ አንድም ችግሩን ከቁጥጥሬ አይወጣም በሚል ስሜት ማቃለልዎት አለያም የውይይት አቅጣጫ ለማስሳቀየስ የተናገሩት ነው የሚመስለው።

አሁንም ደጋግመን የሕግ የበላይነት ይከበር ስንል አንባገነን ሁኑ ወይም የማይገባ እና ያልተመጣጠነ የኃይል እርምጃ ውሰዱ እያልን አይደለም። አጥፊዎች በሕግ አግባብ በወቅቱ ይቀጡ፣ መንግስት ያለውን ሰፊ መዋቅር ተጠቅሞ የቅድመ አደጋዎች እና ግጭቶች የመከላከያ እቅድ ነድፎ ይንቀሳቀስ፣ አደጋዎች መኖራቸው ሲገለጽ ዳር ቆማችሁ ይለይለት በሚመስል መንገድ ስትመለከቱ ከቆያችው በኋላ ተጎጂዎችን ማጽናናት እና ለቅሶ መድረስ ጥቅም የለውም። መንግስት የዜጎችን ደህንነት እና መብት የመጠበቅ እና የማስጠበቅ ግዴታውን ማክበር አለበት። ሕግ ሲጣስ ትዕግስተኛ መሆነ ግን ለጊዜው ወንበራችሁን ባይነቀንቀውም ሕዝቡን ግን የህይወት እና የንብረት ዋጋ እያስከፈለው መሆኑ ልታጤኑት ይገባል።

አሁንም የሕግ የበላይነት ይከበር!