May 29, 2020

Source: https://ethiothinkthank.com/2020/05/29/misusing-the-terrible-story-of-torture-victims-by-yared-hailemariam/

1ኛ/ የዚህ ሰቆቃ ከፊል የሚሆነውን ክፍል ከአመት በፊት መሰለኝ እንዲሁ ለፖለቲካ ፍጆታ በመንግስት ሚዲያ ቀርቦ ተመልክቼዋለሁ። ያኔም የተሰማኝን ጥልቅ ቅሬታ ጽፌያለሁ።

2ኛ/ ይህ ሰቆቃ በቴሌቭዥን ከተላለፈ በኋላ ግን የሰቆቃውን ሰለቦች ዞር ብሎ ያያቸው አካል እንደሌለ አውቃለሁ። እንደውም አንዳንዶቹ አስቸኳይ የአካል እና የአዕምሮ ህክምና ያስፈልጋቸው ስለነበር ለነፍሳቸው ያደሩ ኢትዮጵያውያን በሶሻል ሚዲያ ባሰባሰቡት ገንዘብ መጠነኛ ድጋፍ ሊያገኙ ችለዋል። ብዙዎች ግን እስከ ዛሬ ድረስ አስተዋሽ አጥተው እየማቀቁ ይገኛሉ፣

3ኛ/ የእርቅ እና እውነት አፈላላጊ ተብሎ የተሰየመው አካልም እነዚህን ጉዳዬች መርምሮ የውሳኔ ሀሳብ ይዞ ይመጣል ብለን ብንጠብቅ የውሃ ሽታ ሆኖ ቀረ፣

4ኛ/ መንግስትም የእነዚህን ግፋአን ጉዳይ ከፍትህ ይልቅ ከህውኃት ጋር ለገጠመው ብሽሽቅ እንደ ጨዋታ ማድመቂያ ሲጠቀምበት እያየን ነው።

እነዚህ የኢህአዴግ አስነዋሪ ተግባር እና የሰቆቃ ሰለባዎች ፍትህን ይሻሉ፣ ህክምና ይፈልጋሉ፣ ለጉዳታቸውም ካሳን ይሻሉ። ለዚህም ነው ደጋግመን ፍትህን ያማከለ እና እውነት ላይ የተመሰረት የእረቅ ሂደት – Accountability, truth and reconciliation ይች አገር ያስፈልጋታል እያልን የምንጮኸው።

ገዢው ፖርቲ ትላንት ሰቆቃ በመፈጸም፤ ዛሬ ደግሞ የስቃይ ሰለባዎችን ቁስል እየጎፈደረ ለፖለቲካው ብሽሽቅ ሲጠቀምበት ማየት ልብ ያደማል።

ኢትዮጵያ እውነተኛ የሽግግር ጊዜ ፍትህ (transitional justice) እና የእርቅ ሂደት (reconcilation) ትፈልጋለች። እስከዛው በግፋአን ስቃይ እና እንባ መቆመሩ ቢበቃ ጥሩ ነው።

ፀሃፊ፦ ያሬድ ሃይለማርያም (የሰብዓዊ መብት ተሟጋች)