Saturday, 30 July 2016 11:21
Written by  መታሰቢያ ካሳዬ
 – ትላንት በልደታ ክ/ከተማ 5 ተጠርጣሪዎች ተይዘዋል

– ወንጀሉ ላለፉት 5 ዓመታት በከተማዋ በድብቅ ሲፈፀም ቆይቷል
– እንጀራው 30 በመቶ ጤፍ፣ 70 በመቶ ጀሶና ሰጋቱራ ተቀላቅሎ ይጋገራል
– ሀኪሞች፤ ጀሶና ሰጋቱራ በጉበትና ኩላሊት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያደርሳል አሉ
– በሁሉም ክፍለ ከተሞች ድርጊቱ እንደሚፈፀም ለማወቅ ተችሏል

            የጤፍ ዱቄትን ከጀሶና ሰጋቱራ ጋር ቀላቅለው እንጀራ የሚጋግሩ በየአካባቢው እየተያዙ ነው

በአዲስ አበባ ከተማ የተለያዩ ክፍለ ከተሞች ጥቂት የጤፍ ዱቄትን ከጀሶ፣ ከሰጋቱራና ከደረቀ እንጀራ ዱቄት ጋር በመቀላቀል እየጋገሩ፣ ለገበያ የሚያቀርቡ ሰዎች ከየአካባቢው በቁጥጥር ሥር እየዋሉ ነው፡፡ እስከ አሁን በአቃቂ ቃሊቲ፣ በልደታ፣ በንፋስ ስልክ ላፍቶና በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተሞች እንዲሁም በሰበታ ከተማ ውስጥ በተመሳሳይ ድርጊት ላይ የተሰማሩ ህገወጦች መያዛቸው ታውቋል፡፡ በትላንትናው ዕለት በልደታ ክ/ከተማ በተመሳሳይ ድርጊት ላይ የተሰማሩ 5 ተጠርጣሪዎችን ፖሊስ በቁጥጥር ስር አውሏል፡፡
ህገወጦቹ 30 በመቶ የጤፍ ዱቄት፣ ቀሪውን 70 በመቶ ደግሞ ጀሶ፣ ሰጋቱራና የደረቅ እንጀራ ዱቄት በመቀላቀል እየጋገሩ ለሆቴሎች፣ ለሱፐር ማርኬቶች፣ ለሱቆችና ለምግብ ቤቶች በስፋት ሲያከፋፍሉ ቆይተዋል፡፡ ድርጊቱ በከተማዋ በሁሉም ክፍለ ከተሞች እየተፈፀመ እንደሚገኝና የተፈጨውን ሰጋቱራና የጀሶ ዱቄት ግብአቶች የሚያቀርቡ ግለሰቦች በስፋት እንደሚገኙ በቁጥጥር ሥር ከዋሉት ተጠርጣሪዎች መካከል አንዳንዶቹ ተናግረዋል፡፡
መነሻውን አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ያደረገው ይኸው ህገወጦችን በቁጥጥር ሥር የማዋል ሂደት፤ በንፋስ ስልክ ላፍቶ ላፍቶና በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተሞችም ቀጥሎ ሰንብቷል፡፡ ሰሞኑን በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ፈጥኖ ደራሽ ፖሊስ እየተባለ በሚጠራው የፖሊስ ካምፕ አካባቢ በሚገኘው የቅዱስ ጳውሎስ ቤተክርስቲያን ግቢ ውስጥ በተመሳሳይ ሁኔታ 13 ሰዎች በቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡ ንብረትነቱ የቤተክርስቲያኑ በሆነውና አንድ ግለሰብ በኪራይ በወሰደው በዚህ ቤት ውስጥ በሰባት በርሜል የተቦካና ለጋገራ የተዘጋጀ ሊጥና በከረጢት ተሞልተው የተቀመጡ ጀሶዎች ተይዘዋል፡፡ ቀደም ሲል በዚሁ ክፍለ ከተማ አየር ጤና፣ ታቦት ማደሪያ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ በተመሳሳይ መንገድ ጀሶና ሰጋቱራውን ከጤፍ ጋር እየተቀላቀሉ በመጋገር ለገበያ ሲያቀርቡ የነበሩ 8 ሰዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውንም የክፍለ ከተማው ፖሊስ አዛዥ ኮማንደር አወል ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ወረዳ አንድ ውስጥ የተከናወነ የዚሁ ጤፍን ከጀሶና ሰጋቱራ ጋር ቀላቅሎ በመጋገር ለገበያ የማቅረብ ወንጀል መርማሪ የሆኑት ዋና ሳጅን ጎሽሜ አገኘሁ እንደገለፁልን፤ የድርጊቱ ፈፃሚዎች በአነስተኛና ጥቃቅን የተደራጁ አምስት ግለሰቦች ናቸው፡፡ ከእነዚህ ተጠርጣሪ ወንጀለኞች መካከል ሶስቱ በቁጥጥር ሥር ሲውሉ ሁለቱ እስከ አሁንም አልተያዙም፡፡ ተጠርጣሪዎቹ መንግስት በሰጣቸው ሼድ (መጠለያ) ውስጥ ጤፍን ከጀሶና ሰጋቱራ ጋር እየቀላቀሉ በመጋገር፣ ለሽያጭ የማቅረብ ሥራን ሲሰሩ ቆይተዋል፡፡ ከአንድ ግለሰብ ለፖሊስ በደረሰ ጥቆማ መሰረት፤ የመሥሪያ ቦታቸው በፖሊስ ሲፈተሽ ለመጋገር የተዘጋጀ 17 በርሜል ሊጥ፣ ከ20 ኩንታል በላይ የተፈጨና ለመቦካት የተዘጋጀ ዱቄት፣ በርካታ የሰጋቱራና የጀሶ ክምር መገኘቱን መርማሪው ገልፀዋል፡፡ በወቅቱ በጋገራውና በሊጥ ማቡካቱ ሥራ ላይ ተሰማርተው የነበሩ 12 ሰራተኞችና 3 የድርጅቱ ባለቤቶች በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ውለዋል፡፡ የወንጀል ፈፃሚ ናችሁ ተብለው በቁጥጥር ሥር ከዋሉት 15 ሰዎች መካከል 12ቱ ሰራተኞች ድርጊቱን የፈፀሙት ታዘው ነው በሚል ከእስር የተለቀቁ ሲሆን ሶስቱ የድርጅት ባለቤቶች ግን በእስር ቆይተው፣ የ50 ሺህ ብር ዋስ ጠርተው ወጥተዋል፡፡ ሁለቱ ተጠርጣሪዎች አሁንም በፖሊስ አለመያዛቸው ታውቋል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ በቁጥጥር ሥር በዋሉበት ወቅት ድርጊቱ በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች እየተፈፀመ እንደሚገኝና ምንም አዲስ ነገር ወይም ወንጀል አለመሥራታቸውን ሲነገሩ ተሰምተዋል፡፡ ለምርት ግብአትነት የሚጠቀሙበትን የጀሶና የሰጋቱራ ዱቄት በአይሱዙ እያመጡ የሚያከፋፍሏቸው ሰዎች እንዳሉም ተጠርጣሪዎቹ ገልፀዋል፡፡ ከእስር የተለቀቁት አስራ ሁለቱ እንጀራ ጋጋሪዎች በወር 3000 ብር ደመወዝ እየተከፈላቸው ሲሰሩ እንደቆዩም ለማወቅ ተችሏል፡፡
በተጠርጣሪዎቹ ላይ የወንጀል ክስ ያቀረበው የሸማቾች ጥበቃ ባለስልጣን፤ ሶስቱ ተጠርጣሪዎች ባዕድ ነገርን ከጤፍ ጋር ቀላቅለው በመሸጥ በሚል ወንጀል ክስ አቅርቦ ሐምሌ 15 ቀን 2008 ዓ.ም ለፍ/ቤት ምስክሮቹን አሰምቷል፡፡ ፍ/ቤቱ የተባለው ባዕድ ነገር በጤና ላይ የሚያስከትለው ጉዳት መጠን ተመርምሮ ማስረጃው እንዲቀርብለት፣ በማዘዝ ለሐምሌ 26 (የፊታችን ማክሰኞ) ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በትናንትናው ዕለት ደግሞ በልደታ ክፍለከተማ ልዩ ስሙ አፍሪካ ህብረት አካባቢ የጤፍ ዱቄትን ከጀሶና ሰጋቱራ ጋር ቀላቅለው እንጀራ እየጋገሩ የሚሸጡ ግለሰቦችም በቁጥጥር ሥር ውለዋል፡፡ ተጠርጣሪዎች ምንም ዓይነት ህጋዊ ፈቃድ ሳይኖራቸው፣ ለአምስት ሆነው በተከራዩት ቤት ውስጥ የጀሶና የሰጋቱራ እንጀራ እየጋገሩ ለሽያጭ ያቀርቡ ነበር ተብሏል፡፡ ፖሊስ በትናንትናው ዕለት በተጠርጣሪዎቹ ቤት፣ ለጋገራ የተዘጋጀ አራት በርሜል ሊጥ እንዲሁም ሶስት ኩንታል ከሰጋቱራና ጀሶ ጋር የተደባለቀ የእንጀራ እህል ይዟል፡፡
በተመሳሳይ ሁኔታም ባለፈው ሳምንት በሰበታ ከተማ ቀበሌ 02 ልዩ ቦታው ዋቶ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ነዋሪ በሆነ አንድ ግለሰብ የጤፍ ዱቄት ከጄሶና ሰጋቱራ ጋር እየተቀላቀለ ተጋግሮ ለሽያጭ ሲቀርብ በፖሊስ መያዙ ታውቋል፡፡ ግለሰቡ በቁጥጥር ስር በዋለበት ወቅት በርካታ በርሜል ለጋገረ የተዘጋጀ ሊጥና ከሰጋቱራና ጀሶ ጋር የተቀላቀለ ዱቄት በቁጥጥር ሥር ውሏል፡፡
ከጀሶ፣ ሰጋቱራና የሻገተ ደረቅ እንጀራ ጋር እየተቀላቀለ የሚጋገረውና ለምግብነት እየዋለ የሚገኘው ‹እንጀራ››፤ በጤና ላይ የሚያስከትለውን ጉዳት አስመልከቶ አስተያየታቸውን እንዲሰጡን የጠየቅናቸው የውስጥ ደዌ ስፔሻሊስቱ ዶክተር አብርሃም ተስፋዬ፤ ሁኔታው እጅግ አስደንጋጭና ሰብአዊነት የጎደለው ድርጊት መሆኑን ገልፀው፤ የከፋ የጤና ችግር ማስከተሉ አይቀሬ ነው ብለዋል፡፡ ‹‹እንጀራው ለምግብነት ቢውል ይህን ዓይነት የጤና ችግር ያስከትላል ለማለት የንጥረነገሮቹን ምንነት ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ በጥቅሉ ግን በጀሶ ውስጥ የሚገኘው ንጥረ ነገር፣ ነገሮችን የማኮማተር፣ የማጨማደድ ባህርይ አለው፡፡ በዚህ ሳቢያም ሰውነታችን ሊጨማደድና፣ የመጠን ለውጥ ሊያመጣ ይችላል፡፡ ንጥረ ነገሩ፣ በኩላሊት፣ ጉበትና በጨጓራ ላይ የሚያስከትለው የጤና ችግር በቀላሉ የሚገልፅ አይደለም ብለዋል፡፡
የቶም ከፍተኛ ክሊኒክ ባለቤት የውስጥ ደዌ ስፔሻሊቱ ዶ/ር አሚር መርዋን በበኩላቸው፤ ባዕድ ነገሮችን ወደ ሰውነታችን ውስጥ በሚገቡበት ወቅት እንደየ ንጥነገራቸው፣ ይዘታቸውና መጠናቸው የተለያዩ የጤና ችግሮችን ማስከተላቸው አይቀሬ መሆኑን ገልፀው ለባዕድ ነገሮቹ ተጋላጭነታችን እየጨመረ በሄደ መጠን የጉዳታችንም ልክ በዛው መጠን እየጨመረ እንደሚሄድ ተናግረዋል፡፡
‹‹ጀሶና ሰጋቱራ በአንጀት ውስጥ ገብተው መፈጨት የማይችሉ ከመሆኑም በላይ በጀሶ ውስጥ የሚገኘው ኬሚካል፣ የአንጀት ግድግዳን አልፎ ወደ ደም መሄድ ከቻለ፣ በውስጣዊ የሰውነታችን ክፍሎች ላይ ከባድ ጉዳት ያስከትላል፡፡ ለዚህ ደግሞ የመጀመሪያው ተጋላጭ ጉበታችን ነው፡፡ ጉበት በተፈጥሮው ጎጂና መርዛማ ነገሮች በደም አካማኝነት አልፈው ወደ ኩላሊትና ሳንባ እየሄዱ ጉዳት እንዲያስከትሉ የማድረግ ተግባር ያለው በመሆኑ፣ እነዚህ ኬሚካሎችን በሚያገኝበት ጊዜ ራሱን መስዋእት አድርጎ፣ ይዘቱን እንዲቀይሩ ያደርጋቸዋል፡፡ በዚህ ሣቢያም ጉበታችን ለጉዳት ይጋለጣል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ከጉበት አቅም በላይ ከሆነ ወደ ኩላሊት በመሄድ የኩላሊት ጠጠርና መሰል ችግሮች እንዲከሰቱ ያደርጋል፡፡ በእንጀራው ውስጥ የሚጨመር የሻገተ እንጀራ ደግሞ አፍላቶክሲን በተባለው ንጥረ ነገር አማካኝነት ጉበት ላይ ጉዳት ያደርሳል፡፡ ይህ ደግሞ የገቡት ካንሰርን ሊያስከትልም ይችላል›› ብለዋል ዶ/ር አሚር፡፡

አዲስ አድማስ

Leave a Reply