–  በሐሮማያና በባህር ዳር መምህራን ከተሳትፎ ታቅበዋል

 –  በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ውይይቱ አልተጀመረም

መንግሥትና ገዥው ፓርቲ በትምህርት ዘርፍና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ዙሪያ ከዩኒቨርሲቲ ማኅበረሰብ አባላት ጋር የጀመረው ውይይት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህራንና የዩኒቨርሲቲው አስተዳደር አባላት ከፍተኛ ተቃውሞ ገጠመው፡፡

በአገሪቱ በሚገኙ 35 ዩኒቨርሲቲዎች ውይይቱ የተጀመረው ባለፈው ሳምንት ውስጥ ሲሆን፣ በአዲስ አበባና በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲዎች ውይይቱ የተጀመረው መስከረም 9 ቀን 2009 ዓ.ም. ነው፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ውይይቱ በአምስት ቦታዎች ተከፍሎ የተካሄደ ቢሆንም፣ ዋናውና በዩኒቨርሲቲው ቦርድ ሊቀመንበር አቶ ካሣ ተክለብርሃን የተመራው ውይይት የተካሄደው በብሔራዊ ስብሰባ ማዕከል ነው፡፡በዚህ ውይይት ላይ በርካታ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ማኅበረሰብ አባላት ተገኝተዋል፡፡ ውይይቱን የሚመሩት የዩኒቨርሲቲው ቦርድ ሊቀመንበርና የፌዴራልና የአርብቶ አደር ጉዳዮች ሚኒስትሩ አቶ ካሣ ተክለብርሃንና የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንትና ምክትል ፕሬዚዳንት በቀጥታ ወደ ውይይቱ አጀንዳዎች ለመግባት በሞከሩበት ወቅት፣ ከፍተኛ ተቃውሞ ከዩኒቨርሲቲው መምህራን ገጥሟቸዋል፡፡

‹‹እናንተ ውረዱና ከእኛ ጋር ተቀመጡ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይምጡና ያወያዩን፤›› ሲሉ አንድ መምህር ጠይቀዋል፡፡

‹‹የዛሬ ዓመት በተመሳሳይ የውይይት መድረክ ብዙ ቁም ነገሮች ተነስተው ነበር፡፡ ነገር ግን አንዳቸውም ሳይተገበሩ ዛሬ ደግመን ተገናኘን፤›› ሲሉ ውይይቱ ፋይዳ ቢስ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ ሌሎች አስተያየት ሰጪዎች ደግሞ በቀጥታ በአወያዮቹ ላይ ያነጣጠረ ትችት ሰንዝረዋል፡፡

‹‹አቶ ካሣ እርስዎ ሚኒስትር ነዎት፡፡ በዚያ ላይ የዩኒቨርሲቲዎችን ቦርድ ሊቀመንበርም ነዎት፡፡ በዚህ ሁሉ ኃላፊነት ውስጥ ሆኖ በዩኒቨርሲቲው የዶክትሬት ተማሪ መሆን አይቻልም፡፡ ስለዚህ ሥራዎትን ይልቀቁ፤›› ሲሉ አንድ መምህር ጠይቀዋል፡፡

ሌላው መምህር በበኩላቸው፣ ‹‹የመንግሥት ሥልጣን ይዘው ለግል ጥቅም በማዋል የዩኒቨርሲቲውን ሕግ ጥሰው የዶክትሬት ተማሪ ሆነዋል፤›› ሲሉ ተችተዋል፡፡

ለተነሱባቸው ትችቶችና ተቃውሞዎች ምላሽ የሰጡት አቶ ካሣ፣ መንግሥት ወክሏቸው በኃላፊነት ውይይቱን ለመምራት መምጣታቸውን፣ ይህ ማለት ግን ከተወያዮቹ የተሻሉ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡

‹‹እኔ ብማር ክፋቱ ምንድነው? እኔም እኮ አንድ ዜጋ ነኝ፡፡ ከዚህ ቀደም እኔም ትምህርት የመጀመሩን ዕድል አግኝቼው ነበር፤›› ሲሉ ተረጋግተው መልሰዋል፡፡

ከዚህ በኋላ የተሻለ መረጋጋት የተስተዋለ በመሆኑ ወደ ውይይቱ አጀንዳዎች ለመግባት ሲሞከር አንድ መምህር በማሳሰቢያ መልክ፣ ‹‹በመጀመሪያ ይኼ ስብሰባ ሲጀመር በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በጋምቤላና በኮንሶ ለተገደሉ ንፁኃን ዜጎች የአንድ ደቂቃ የህሊና ፀሎት ሊደረግ ይገባል፤›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡

ይህንኑ ተከትሎም መድረኩን የሚመሩት አወያዮች የህሊና ፀሎት አስደርገዋል፡፡ በመቀጠል የውይይቱ የመጀመሪያ አጀንዳ የሆነው፣ ‹‹የማሽቆልቆል ምዕራፍ ተዘግቶ የዕድገት ምዕራፍ በተከፈተበት የሃያ አምስት ዓመታት ጉዞ ውስጥ የከፍተኛ ትምህርት ሚናና ለቀጣይ ተልዕኮ ሊኖረው የሚገባ ቁመና›› በሚል ርዕስ የተዘጋጀው ሰነድ ቀርቧል፡፡

ይሁን እንጂ በዚህ ሰነድ ላይም ለመወያየት ፍላጐት አልታየም፡፡ ‹‹ሰው እየሞተና ሕዝብ ለተቃውሞ እየወጣ አገሪቱ የፖለቲካ ቀውስ ውስጥ ገብታ ስለትምህርት ጥራትና ተደራሽነት መወያየት ያሳፍረኛል፤›› ሲሉ አንድ መምህር ተናግረዋል፡፡

ሌላ ተናጋሪ በበኩላቸው አቶ ካሣን ጨምሮ የዩኒቨርሲቲው አመራሮች ብቁ አይደሉም በመሆኑም ይልቀቁ ሲሉ ጠይቀዋል፡፡

ሰነዱ ‹‹ትምህርትና የኢትዮጵያ ሁኔታ፣ ያለፉት 25 ዓመታት በአገሪቱ የተመዘገቡ አንኳር ለውጦች፣ የማሽቆልቆል ጉዞን በገታ ሩብ ምዕተ ዓመት የልማት፣ የሰላምና ዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ አገራዊ ስኬት ውስጥ የከፍተኛ ትምህርት ሚና›› የሚሉና ሌሎች ንዑስ ርዕሶችን ያካተተ ነው፡፡

በርካታ መምህራን ውይይቱን በመሰልቸት ጥለው ወጥተዋል፡፡ በማግሥቱ የተወያዮች ቁጥር በእጅጉ በመሳሳቱ ወደ ቡድን ውይይት በዲፓርትመንት እንዲካሄድ ተወስኖም ውይይቱ ተበትኗል፡፡

በተመሳሳይ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ላይ በሐሮማያ ዩኒቨርሲቲ የተጀመረው ውይይት ቀናትን ያሳለፈ ቢሆንም፣ መምህራን በአካል ከመገኘት ባለፈ ተሳትፎ እያደረጉ አለመሆኑን ምንጮች ገልጸዋል፡፡

በዚህ የተነሳም ውይይቱን እንዲመሩ የተወከሉት የዩኒቨርሲቲው ቦርድ ሊቀመንበር አቶ ስለሺ ጌታሁንና አቶ ሴኮቱሬ ጌታቸው፣ የመምህራኑ ዝምታ እንዲጠና ሲሉ ሐሳብ አቅርበው ኮሚቴ ተቋቁሟል፡፡

በተመሳሳይ በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ መስከረም 9 ቀን 2009 ዓ.ም. ቢጀመርም መጠነኛ ተሳትፎ ብቻ ታይቷል፡፡ መስከረም 10 ቀን በነበረው ውሎ አንድም አስተማሪ ጥያቄ አለማቅረቡን ምንጮች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

ውይይቱን የመሩት የቦርድ ሰብሳቢው አቶ አለምነው መኮንን፣ በዩኒቨርሲቲው መምህራን በተደጋጋሚ በቀረበው ማጉረምረምና ዝምታ ደስተኛ ሳይሆኑ ስብሰባውን እየመሩ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በጎንደር ዩኒቨርሲቲ መጀመር የነበረበት ውይይት እስከ ማክሰኞ መስከረም 11 ቀን 2009 ዓ.ም. አለመጀመሩን የሪፖርተር ምንጮች ገልጸዋል፡፡

በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ውይይትን እንዲመሩ የተመደቡት የቦርድ ሊቀመንበሩ ዶ/ር ስንታየሁ ወልደ ሚካኤል ሲሆኑ፣ ዶ/ር አምባቸው መኮንንና ሌሎች አምስት የኢሕአዴግ አባላትም ተወክለዋል፡፡

በመቀሌ ዩኒቨርሲቲም የመምህራኑ ውይይት የተጀመረው ባለፈው ሐሙስ ሲሆን፣ ውይይቱን የመሩት የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንትና የሕወሓት ሥራ አስፈጻሚ አባል ዶ/ር አዲስዓለም ባሌማ ናቸው፡፡ በውይይቱ ወቅትም አንድ መምህር፣ በመገናኛ ብዙኃን መንግሥት የሚናገረው ምንም ረብ የሌለውና አሰልቺ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ አወያዩ ምንም አዲስ ነገር እንደማይናገሩም ገልጸው፣ ምሁራንን አዳምጠው ማስታወሻ በመያዝ ከመንግሥት ጋር እንዲወያዩበት ጠይቀዋል፡፡

በመፈቃቀድ ላይ የተመሠረተ ዴሞክራሲ ለአገሪቱ ህዳሴ ያለውን ወሳኝ አስተዋጽኦ ሁሉም ወገን ተረድቶ ብዝኃነትን ለማስተናገድ ለብሔራዊ መግባባት መሠረት መፍጠር የውይይቱ ዓላማ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በውይይቱ ማጠናቀቂያ ላይ የዩኒቨርሲቲ አመራሮችና ፈጻሚዎች ሚና በዝርዝር የሚገመገምበት ሂስና ግለሂስ እንደሚደረግም ለዩኒቨርሲቲዎቹ ከተላከው ሰነድ ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡

አዲስ ገቢ ተማሪዎች ብቻ ደግሞ ‹‹ሕገ መንግሥታዊ መርሆዎችና ሰላማዊ የትግል ሥልት በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት›› በሚል ርዕስ ውይይት እንደሚያካሂዱ ታውቋል፡፡

በአጠቃላይ የተጀመረውን ውይይትና ሥልጠናውን የሚከታተል ከኢሕአዴግ ምክር ቤት ጽሕፈት ቤትና ከትምህርት ሚኒስቴር የተውጣጣ ኮማንድ ፖስት ተቋቁሟል፡፡

በየዩኒቨርሲቲው የተደራጁ አስተባባሪ ኮሚቴዎች ዕለታዊ የመገምገሚያ ነጥቦች መሠረት ውሎአቸውንና ሳምንታዊ እንቅስቃሴያቸውን ገምግመው ለክልል በየዕለቱ የስልክ ሪፖርትና በየሳምንቱ የጽሑፍ ሪፖርት እንዲያደርጉ መታዘዛቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡

ክልሎች በበኩላቸው ከየዩኒቨርሲቲዎቹ የሚደርሷቸውን ሪፖርቶች አደራጅተው በየዕለቱ በስልክ እንዲሁም በየሳምንቱ በጽሑፍ ወደ ማዕከል ሪፖርት እንዲያደርጉ መታዘዛቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በአጠቃላይ ትምህርት የሚጀመረው ከጥቅምት 1 ቀን 2009 ዓ.ም. በኋላ እንደሆነም ሰነዱ ይገልጻል፡፡